Sunday, April 21, 2013

ድሀውን ያልጠቀመ እድገት?! ክፍል 2


ሁለተኛው የመልሴ የማብራርያ ክፍል በማህበራዊና ዘርፍና በመሰረተ ልማት ግንባታ ላይ የተገኙ ውጤቶችን ተመርኩዞ እንደሚከተለው ተሰናድቷል$ መልካም ንባብ$

ማህበራዊ ለውጦች እንደ እድገቱ ማሳያ
ሀገራችን ባለፉት አመታት ካሳየቻቸው ለውጦች ውስጥ መጠቀስ ያለባቸው ትላልቅ ስራዎች በኔ እይታ የማህበራዊ ዘርፉ ስራዎች ናቸው$ በተለይም ደግሞ ትምህርትና ጤና ያሳዩት ለውጥ$ ሶማሌ አፋር ጋምቤላና ቤኒሻንጉልን ትተን የሀገራችን የትምህርት የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ሽፋን መቶ በመቶ ሊባል በሚችል ደረጃ ተሳክቷል$

እየተነሱ ያሉ መሻሻል ያለባቸው የጥራት ጉድለቶች እንደተጠበቁ ሆነው ስለ ትምህርት የማይታሰብባቸው ገጠራማ አካባቢዎች በቅርባቸው ትምህርት ቤት እያገኙ ከመቆፈር የተለየ ስራ የማግኘት እድላቸውን ከማስፋትም በላይ ያንኑ የእርሻ ስራም ቢሆን በተሻሉ አሰራሮች የመምራት አቅሙና የአዲስ ቴክኖሎጂ አቀባበሉ የተሻለ ዜጋ በመፍጠር ረገድ ትምህርት ያለው ፋይዳ የላቀ ነው$ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የተማረ ህዝብ መብቱን የመጠየቅ የአካባቢዉን መሪዎች የመሞገት የመገምገም ጥቅሞቹን የማስጠበቅ አቅሙን እንዲያሳድግ ማድረግ የሚያስችል ስለመሆኑ ጥርጥር የለውም$ አንዳንዶቹ ለውጦች በ10 አመትና በዚያ ግዜ የምናያቸው ባለመሆኑ ጉልህ ባይሆንም ጥንስሳቸው ግን የሚጭበረበር አይመሰለኝም$

ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን በየአካባቢው በማዳረስም ረገድ ከፍትሀዊነትም ይሁን ከብዛታቸው አንጻር የሚታየው ለውጥ በጎ የሚባል ነው$ ይሄ በየአካባቢው የስራ እድል ከመፍጠሩም በላይ በገበያና አካባቢውን በማነቃቃት ረገድ ያለው ሚና ቀላል አደለም$

በሚለንየሙ ግቦች ማብቂያ ግዜም ሀገራችን ከስምንቱ ግቦች ስድስቱን ማሳካት ከሚችሉ ወጤታማ ሀገሮች መካከል አንዷ መሆኗ ይታወቃል$ ሁለቱ በዚሁ ግዜ የማይሳኩት የእናቶችና የህጻናትን ሞት የሚመለከቱት ግቦች ናቸው$

በርግጥ በዚህም ረገድ ሀገራችን የሞቱን ቁጥር ከግማሽ በላይ መቀነስ የቻለች ቢሆንም ወደ ውጭ ጉዳይ ሚንስትርነት ሳይሄዱ በፊት ዶር ቴድሮስ እንዳሉት ለውጡ ግዙፍ ቢሆንም ዛሬም ቢሆን የሞቱ መጠን ትልቅ ስለሆነ ስራው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ይታወቃል$ በለውጡ መደሰታችን ባይቀርም የቀረንን ጉዞ ጨርሰን አንድም እናት በውልጃ ምክንያት አትሞትም የሚለውን ህልማችንን ማሳካት ይኖርብናል$ ይሄ ሀገሪቱ ከእድገቱ የተገኙ ተጫማሪ ሀብቶችን የማህበረሰቡን ጤና ለማሻሻል እያዋለች ስለመሆኑ ያመላክታል$ በቅርቡ ከወሊድ ጋር የተያያዘ ማንኛውም የመንግስት ጤና ጣብያ የማዋለድ አገልግሎትን ጨምሮ ነጻ እንዲሆን መደረጉ የዚሁ ጥረት አንድ ክፍል መሆኑን ማየት ይቻላል$

በቀላሉ መከላከል በሚቻሉ በሽታዎች ይሞት የነበረውን ዜጋ ለመከላከል በሀገር አቀፍ ደረጃ የተሰማሩት ከ34 ሺ የሚልቁ የጤና ኤክስቴንሽን ሰራተኞች በመታጠብ መዳን መጸዳጃ ቤት በመስራት መዳን የአመጋገብ ስርአትን በማሻሻል መዳን የእርግዝና ክትትል በማድረግ መዳን በጤና ጣብያ በመውለድ መዳን እንደሚቻል ያሳዩና በዚሁ ጥረት በርካታ ዜጎች በቀላሉ መከላከል በሚቻሉ በሽታዎች እንዳይሞቱ የተሰራው ስራ በተለያዩ አለማቀፍ መድረኮች በአለማቀፍ በጎ አድራጊ ድርጅቶችም ሳይቀር የተሞካሸ ነው$ በመሆኑም ይሄ ከእድገቱ የተገኘውን ፍሬ 83 በመቶ ለሚሆነው ድሀውና ገጠሬው ሀገሬ በማዳረስ ረገድ የተሰራው ስራ ውጤታማ መሆኑን ያመላክታል$

ከዚህ ሌላም በማህበራዊ ዋስትና ረገድ እየተፈጸሙ ያሉ ስራዎችም ተስፋ ሰጪ ናቸው$ አንደኛ በሴፍቲኔት ረገድ የተለመደውን እህልና ገንዘብ የማደል አዝማሚያ በመቀየር ሰፊ የአካባቢ ጥበቃ ስራ ማካሄድ በድርቅ በተደጋጋሚ የሚጠቁ አካባቢዎች ቋሚ ትምህርት ቤት ጤና ጣብያ ውሃ እና ሌሎች አስተዳደራዊ መዋቅሮች እንዲኖሯቸው በማድረግ አካባቢዎቹ በዘላቂነት የሚያጋጥሟቸውን ተደጋጋሚ ችግሮች እንዲቋቋሙ ለማድረግ እየተሰራ ያለው አፈጻጸምም ይቀጥል ያሰኛል$

በመሆኑም ይሄም የሚሰጠው አመራር ወጤታማ እንደሆነና እድገቱ በፍትሀዊነት መከፋፈል የቻለ መሆኑን ያመላክታል$ ከዚህ ውጪም መንግስት በአቅሙ ለአደጋ የተጋለጡ ዜጎችን ለማገዝ በሙከራ ደረጃ ከተለያዩ አለማቀፍ ድርጅቶች ጋር በትብብር እየሞከራቸው ያሉ ፕሮግራሞች አሉት$ በሂደት እነዚም ቢሆኑ መንግስት 1 በመቶ የታክስ ገቢውን በጅቶ ሊፈጽማቸው የሚያስባቸው በመሆኑ የሚበረታቱ ናቸው$ ይሄም እድገትን ለድሀውና ለማህበራዊ ችገሮቹ መፍቻነት በማድረግ ረገድ የሚታዩትን ለውጦች የሚያመላክት ነው$

ይህ ሁሉ ሆኖ ግን ዛሬም ችግሮቿን አሟጣ ለመፍታት ካላት የህዝብ ብዛት አንጻር ረጅም መንገድ መጓዝ ያለባት ሀገር መሆኗን የሚያመላክት እንጂ የማዘናግያ ደወል አደለም$ ለውጥ እያመጣ ያለ ስራ መኖር የችግሮች ተሟጦ ማለቅ አዋጅ ተደረጎ መቅረብ የለበትም ልክ ለውጡ በዚያ እየተሳበበ መካድ እንደማይኖርበት ሁሉ$

የመሰረተ ልማት ግንባታ
የመንገድ መብራት የማመጨትና የቴሌኮም ማስፋፍያ ስራዎች ከፈጠሩት የስራ እድል ካነቃቁት እና ካሰማሩት በርካታ ቢዝነሶች አኳያ ሲለካ እድገቱ በዘላቂ ዘርፎች ላይ እንዲያተኩር መደረጉን የሚያመላክት ስለመሆኑ አያጠራጥርም$ መንገዶቹ አንደኛ የትራንስፖርት ዘርፉን በማሳለጥ ረገድ ያስገኙት ጥቅም ሁለተኛ የንግድ ስራውን እና የአርሶ አደሩን ምርት ወደ ተጠቃሚው በማድረስ ረገድ የላቀ ሚና ያላቸው ናቸው$

ባንድ በኩል የመንገድ ስራውን ማካሄድ የሚችሉ ሀገራዊ ኮንትራክተሮችንና ባለሞያዎችን በማፍራት ሀብት መፍጠር የተቻለ ሲሆን በዚያው ሂደት የተሰሩት በሺዎች ኪሎሜትሮች የሚቆጠሩ መንገዶች ለሀገሪቱ ዘላቂ ልማት መፋፋም ወሳኝ የሆኑ አቅሞች ከመፍጠር ጎን ለጎን በዛሬውም ግዜያዊ ውጤቱ ትልቅ ሀገራዊ መነቃቃት የፈጠሩ ናቸው$ በርግጥ ይሄ በቀጥታ ወደያንዳንዳችን ኪስ የሚገባ ገንዘብ አይሆንም$ ግን እንቅስቃሴያችንን ቀላል በማድረግ ረገድ የራሱ ሚና አለው$

ቴሌኮሙ መስፋፋቱ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚኖረንን መረጃ ፈጣን ከማድረጉም በላይ በመላ ሀገሪቱና በአለም ዙርያ የሚከናወኑ ነገሮችን ለመከታተል የሚያሰችል በመሆኑ የማህበረሱቡን አስተሳሰብና ውሳኔ መረጃ ቀመስ በማድረግ ረገድ ላቅ ያለ ሚና ይኖረዋል$

በየገጠሩ እየገባ ያለው የመብራት አገልግሎትም ማህበረሰቡን ከኩራዝ ከመገላገሉም በላይ በየአካበቢዎቹ ቢዝነስ በማነቃቃት ረገድ የሚኖረው ሚና የላቀ መሆኑ አይቀሬ ይሆናል$ ይሄ ወደ ገንዘብ ሀብት ወደማፍራት በሂደት የሚመነዘር ይሆናል$ በየወረዳው እየገባ ያለው መብራት በርግጥም በዚህ አገር አገልግሎትን ለከተማና ለገጠር ያለ አድሎ የማቅረቡን አሰራር ይበልጥ እያጠናከረው የሚሄድ ነው$

በርግጥ ከነኬንያ አንጻር ሲታይ ሀገራችን በቴሌኮም ረገድ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት የማቅረብ ችግር ቢኖርባትም ቴሌኮምን እንደ ልማት አንድ አብይ መሳርያ በመላው ሀገሪቱ በማዳረስ ረገድ ግን በማንኛውም መመዘኛ ጥሩ ስራ እየሰራ ያለ መሆኑን ያመላክታል$ ይሄ ስኬቱ ግን የድክመቶቹ መደበቂያ መሆን አለበት ማለቴ አደለም$

የሆነ ሆኖ ቴሌኮምን የከተሜው ብቻ እንዳይሆን በማድረግ በመላው ሀገሪቱ እንዲዳረስና ሁነኛ የልማት አቅም በማድረግ ረገድ የተገኘው ውጤት አበረታች ነው$ በቅርብ ያገኘሁት መረጃ እንደሚያመለክተው ቴሌ በሞባይል እንኳ ወደ 20 ሚሊየን ገደማ ደንበኞች ያፈራ መሆኑ ይታወቃል$ በቴሌ በሚቀጥሉት ሁለት አመታት የሞባይል ደንበኞች ብዛት ከ40 ሚሊዮን በላይ እንደሚሆን ግምቶች ያመላክታሉ$

እነዚህ ለውጦች በዘርፉ እየተደረገ ያለው ኢንቨስትመንት ማህበረሰቡ የተሻሉ የመገናኛ አገልግሎት እንዲኖረው ለማድረግ መንግስት እያወጣ ያለውን በቢሊዮኖች የሚቆጠር ኢንቨስትመንት የሚያሳይና ከለውጡ አብዛኛው ገጠሬ ኢትዮዽያዊ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተደረገ ያለውን ያላሰለሰ ጥረት የሚያሳይ ነው$ በዚሁ የቴሌ የማሰፋፍያ ስራ ከሚፈጠረው ገቢ ውጭ ከቴሌ ጋር ተከያያዙ ሽያጮች ቀላል የማይባል ገቢ እያገኙ ያሉ መኖራቸው አወያይ አደለም$ ከሞባይል ስልክ መሸጫ ጀምሮ በሲም ካርድና በአየር ሰአት ካርድ ሽያጭ የሚገኘው ገቢ ቀላል አደለም$ ለዚያም ነው በርካታ አለማቀፍ የሞባይል አምራች ድርጅቶች የሀገሪቱን የሞባይል ገበያ እየተሻሙት የሚገኙት$

በማብራት ሀይል ማመንጨት ረገድም ሀገሪቱ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ማሟያነት ከመስራትም አልፋ ለአካባቢው ሀገሮች የሀይል ምንጭ ለመሆን እያከናወነች ያለችው ትላልቅ የውሀ ሀይል ግድብ ግንባታዎች በአካባቢው ብቻ ሳይሆን በአፍሪካም ደረጃ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው ስለመሆኑ መረጃዎች ይጠቁማሉ$ በአሁኑ ወቅት ጊቤ 3 እና ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ሀገሪቱ ከመብራት ሀይል ወደ 7 ሺ 800 መቶ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሀይል ለማመንጨት እየሰራች መሆኑ ይታወቃል$ 

የንፋስና ሌሎች ትናንሽ የውሃ ሀይል ማመንጫዎችን ደምረን ስናስብ ከስምት ሺ ሜጋ ዋት በላይ የመብራት ሀይል በሚቀጥሉት 5 አመታት ውስጥ እንደሚለማ ይታወቃል$ በሚቀጥሉት ሁለት አመታት ውስጥ እስከ 2000 ሜጋ ዋት የሚደርስ ሀይል ለአገልግሎት እንደሚደርስ አንዳንድ ግምቶች ያሳያሉ$ በፈጠረው የስራ እድል እንኳ ሲመዘን የመብራት ሀይል የማመንጨት ስራው በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ የስራ እድሎች መፍጠር የቻለ ነው$

ከዚያም በላይ ባሰገኘው የእውቀት ሽግግር ሲመዘን ትልቅ ግምት የሚሰጠው ሀገራዊ አቅም እንደፈጠረ መመልከት ይቻላል$ ለዚህ ዋነኛው ማሳያ በጊቤ 2 እና በበለስ ሀይል ማመንጫ ስራ ላይ የተሳተፈው የሰው ሀይል በግዙፉና ውስብስቡ የህዳሴ ግድብ ላይ ያንን ልምድና ክህሎት ይዞ የተሰለፈ መሆኑና ስራውን በተሳካ መንገድ እየመራ መሆኑ ነው$

ደሀውን ያልጠቀመ እድገት?! ክፍል 1


ማስተዋል ደሳለው በፌስቡክ ፔጁ የሀገራችን እድገት የኑሮውድነቱን እንዳላቃለለና ለደሀው ያመጣው የረባ ለውጥ ስላለመኖሩ ወቅሷል$ ያነሳው ገንቢ ክርክር ነው ብዬ ስላመንኩ እድገቱ ሰብአዊ ልማት እያመጣ ያለና እና ደሀውን እየጠቀመ ስለመሆኑ ማመላከት ፈልጌ ነው መልስ ፈጻፍ የመረጥኩት$ ሀሳቤን በሁለት ክፍል አቀርባለሁ የመጀመርያው እነሆ

ሲጀመር በደሀውና በሀብታሙ መሀከል ያለው ምጣኔ በአለም የተሻለ ምጣኔ አላት ከሚባልላትም ከቻይና የተሻለ የሚባል ነው$ የቻይና ምጣኔ 0 ነጥብ 38 ሲሆን የሀገራችን ደግሞ 0 ነጥብ 34 እንደሆነ በቅርብ የወጣ የዩኤንዲፒ መረጃ ያመለክታል$ የኢትዮዽያ ማደግ አለማደግ አነጋጋሪ የሆነባቸውን ወቅቶች አለፈናል ተመስገን$ አሁን ያለው ጭቅጭቅ እድገቱ እውነት 11 በመቶ ነው ወይስ ከዚያ በታች እና እድገቱ እነማንን እየጠቀመ ነው የሚለው ነው$

ሀገራችን እድገት እድገት እያስመዘገበች መሆኑ የሚያከራክር አደለም$ ሆኖም ግን በጅምር አካባቢ ምርቱ ሲጨምር አርሶአደሩ በመንገድ እና በትራንስፖርት እጦት ምርቱ ዋጋ ሳያወጣ የቀረበት$ በሌላ ግዜ ደግሞ ድርቅ በሚፈጥረው የምግብ እጥረት ለርሀብ የተዳረገባቸው ግዜዎች ነበሩ$ ኢህአዴግም ወጥ የሆኑ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ዘርፍ እድገት ማስፈጸምያ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ቀርጾ ሀገራዊ ልማትና እድገቱን ያልመራበት የጅምር ወቅቶች ነበሩ$

በኢህአዴግ ደረጃ ታምኖባቸው በውይይት ዳብረው የኢኮኖሚና ማህበራዊ መመርያ የሆኑ ፖሊሲዎች መፈጸም ከጀመሩበት 1995 2005 ዓም ሀገሪቱ ማስመዝገብ የቻለችው ለውጥ በርግጥም አስደሳችና ተስፋ ሰጪ ነው$

እንደ ገንዘብና ኢኮኖሚ ሚንስትርና እንደ አለም ባንክ አይኤምኤፍ እና ዩኤን ያሉ ተቋማት የሀገራችን በጀት ደሀ ተኮርና ድህነትን ለመቀነስ የተነጣጠረ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ይሰጣሉ$ ቁምነገሩ ይሄ ደሀ ተኮር የተባለው አበጃጀትና አፈጻጸም በተግባር የየትኞቹን ድሆች ህይወት ቀይሯል ነው$

ድህነትን ለመቅረፍ ያለመ በጀት
በአፍሪካ ደረጃ በማንኛውም መመዘኛ ሲታይ የሚያስመሰግን ደሀውን የህብረተሰብ ክፍል ለመለወጥ የሚያልም አበጃጀት ነው የምንከተለው$ 70 በመቶ በላይ በጀት ድህነትን ለመቅረፍ በሚያስችሉ ስራዎች ላይ ያተኮረ ነው$ የአንደኛ እና ሁለተኛ እንዲሁም ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግንባታ ዋና ስራው ያደረገ በጀት ነው$ በርግጥ ይሄ ምግብም ልብስም መጠለያም አይሆንም በየትኛውም መስፈርት የዛሬውን ችግር የመቅረፍ ፋይዳ የለውም$

ያን የመሰለውን ሀብት የሚፈጥር አቅም የሚገነባው በትምህርት የተገነባ ማህበረሰብ ያለን እንደሆነ መሆኑ ግን አያጠያይቅም$ በዚያ ሲመዘን ገጠሬውን ደሀውን ለዚያውም ከሰማንያ በመቶ በላዩን ኢትዮዽያዊ የሚቀይር ዘላቂ ስራ በማከናወን ረገድ አጋጥሞታል ከሚባለው የትምህርት ጥራትም ችግር ጋር ቢሆን የላቀ ውጤት እያስገኘ ያለ ስራ ነው$ እናም ድህነትን በመቅረፍ ረገድ መንገድ መጥረጊያ የሆነውን የብርሀን ያክል የሚቆጠረውን መሳርያ ትምህርትን እያስታጠቀ ያለ በጀትና አፈጻጸም በመሆኑ በርግጥም ድህነትን በመቅረፍ ረገድ አመርቂ ስራ እየተሰራ ስለመሆኑ ማሳያ ነው$

ይሄን ድምዳሜ በማንኛውም የዩኤን ተቋማት አለም ባንክና አይ ኤም ኤፍ በኩል የሚወጡ መረጃዎችም ያመላክታሉ$ ይሄን ማለት ያስፈለገኝ የመንግስት ተቋማትን እና ያንን መረጃ የሚቀበሉ አካላት የኢህአዴግን የተጋነነ መረጃ ያንቆረቁራሉ ተብሎ ስለሚታማ ነው$ በኔ እምነት እነዚህ የመንግስት ተቋማት ላለፉት አስርት አመታት ሲያወጧቸው የነበሩ መረጃዎች ትክክል መሆናቸውን በቅርቡ አለም ባንክ የሀገራችንን ኢኮኖሚ በሚመለከት ያወጣው የአስር አመት ሪፖርት ያመላክታል$

በርካታ የአፍሪካ ሀገራት የተሿሚዎቹን ቤት እና የመዝናኛ ወጪ ለመሸፈን በሚሯሯጡበት እንደ ናይጄሪያ ያሉ አገሮች ለመሪዎቻቸው በሚገርም መልኩ እስከ አስር ፕሬዚዴንሻል አውሮፕላን በሚያቀርቡበት በጀት ቅርጫ በሚመስለበት አህጉር በጀቱን በተጨባጭ ድህነትን ሊፈቱ በሚችሉ ዘላቂ የልማት አቅሞች ላይ በማዋል የምትታወቅ ሀገር ኢትዮዽያ ናት$ ይሄ ድምዳሜ ግን ችግሩን መፍታት በሚያስችል አስተማማኝ መንገድ ላይ ስለመሆናችን እንጂ ችግሮች ተፈተው ስለማለቃቸው የሚያሳይ አደለም$

የገጠሩን ታዳጊና ወጣት አይን የሚከፍቱ የማንበብ እና የመጻፍ ክህሎቶችና የተለያዩ የአካባቢ ሳይንስ እውቀቶች የገጠሩን  ማህበረሰብ ከመሬት የመንቀልና በተለያዩ ክህሎቶች በማጎልበት በንግድ እና መሰል ዘርፎች የማሰማራት አቅማቸው ቀላል አይደለም$ ጤናው የተጠበቀለት አብዛኛው ገጠሬም በአመዛኙ በግብርና ኤጀንቶቹ ታግዞ ስራው ላይ የሚያሳልፍ ከሆነ ባለፉት አመታት ያየነው ውጤታማነት ተጠናክሮ የማይቀጥልበት እድል የለም$

ግብርና
ባለፉት አመታት ከአስር በመቶ በላይ እድገት እያሳየ የመጣው የግብርናው ዘርፍ ስኬት ሀገሪቱ እየለማች ስለመሆኑ የገጠሬው ሀገሬ ህይወትም እየተለወጠ ስለመሆኑ ማመላከቻ ነው$ ይሄው ዘርፍ በዚህ አመት እንዳስመዘገበ ከሚታወቀውና ሀገሪቱ እንዲህ አይነት የግብርና እድገት ተቀባይነት የለውም ብላ የተቆጨችበት እድገትም ቢሆን በአፍሪካ ደረጃ ለማሳካት ከተያዘው የስድስት በመቶ እድገት አንጻር ሲመዘን ከፍተኛ የሚባል ነው$ 6 ነጥብ 9 በመቶ ያሰመዘገበችው ሀገራችን ከስከዛሬው የዘርፉ እድገቷ የቀነሰ ቁጥር የመጣ ቢሆንም ቀነሰ የሚባለውም ቁጥር በአፍሪካ ደረጃ ከተያዘው እድገት አንጻር አበረታች ነው$

አንድ በአፍሪካ ደረጃ የግብርና ስኬትን ባለፉት አስር አመታት ምን እንደሚመስል የገመገመ የተጠያቂነት ወትዋች አለማቀፍ ዘመቻ ቡድን ኢትዮዽያ ለግብርናው ዘርፍ ወደ 16 በመቶ በጀት በመመደብ በአፍሪካ በዘርፉ ሻንፒዎን ስለመሆኗ ያትታል$ ከስድሰት በመቶ በላይ እድገትም እንዲገኝ የሚጠይቀውም መስፈርት በማሟላት ቀዳሚዋ አገር መሆኗንም ይመሰክራል$

83 በመቶው ሀገሬ ገጠሬ አርሶ አደር ወይም አርብቶአደር በሆነባት ሀገር ለማደግ ይሄ የህብረተሰብ ክፍል የተሰማራበትን ዘርፍ ማሳደግ የግድ ነው$ በአርሶ አደር አገር ከተሜን ይዞ የትም ድረስ መሄድ አይቻልም$ ቀላሉ የለማ 83 በመቶ 17 በመቶውን ሲቀይረው እንጂ የለማ 17 በመቶ 83 በመቶ የኮሰሰን ገጠሬ ልጎትት ሲል አደለም$ ስለሆነም አርሶ አደሩና አርብቶአደሩ እየተለወጠ ከሆነ አፍ ሞልቶ አገር እየተለወጠ ነው ማለት ይቻላል$

ይሄ ማለት ዘርፉ የተጋረጠበትን ዘመናዊ መሳሪያ የማዘጋጀት የማዳረስ የማስለመድ የምርት ለውጥ በተጨባጭ የማስመዝገብ እና ያንን በየደረጃው እየገመገሙ እያሻሻሉ መሄድ መካድ ማለት አደለም$ የእርሻ ስራውንም በሚቻልባቸው አካባቢዎች ከዝናብ ጥበቃ የማላቀቅ እና በመስኖ እንዲሰራ ማድረግ ሌላው ወሳኝ ስራ ነው$ ይሄ በሚቀጥሉት አመታት ተጠናክሮ ከቀጠለ የተሻሉ ውጤቶች ማየታችን አይቀርም$

የሆነ ሆኖ ህይወቱ እየተቀየረ ስላለ ነው ገጠሬው ቤቱን በቆርቆሮ እየሰራ ልብሱን እየቀረየ የቤት እቃዎች እየሸመተ ወጣ ወጣም እያለ የመዝናናት አዝማሚያም እየተስተዋለበት ያለው$

የቤት ግንባታና ዙሪያ መለስ የስራ እድሎች
ከቤቶች ልማት አንጻር በአዲስ አበባ ብቻ እንኳ የተገነቡ ወደ 140 የሚጠጉ ቤቶች የቤት ችግሩን ከመፍታት አንጻር ካለው ሚናም በላይ በዙርያው ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አነስተኛ እና ጥቃቅን ድርጅቶችን አሰልጥኖ በማሰለፍ ብድር አገልግሎት በመስጠት እቃ በማቅረብ በከተማ አካባቢ ያለውን ሰፊ የስራ አጥነት ችግር በመፍታትም ረገድ ሁነኛ ሚና ተጫውቷል$

ልማቱ ለዜጎች ያስገኘው ጥቅም አለ ለማለት የግድ ሁሉም ማህበራዊ ችግር የቤት ችግር የኑሮ ውድነት መፈታት አለበት ማለት አደለም$ በማንኛውም ሚዛን በመቶ የሚቆጠሩ ቤቶች በአዲስ አበባ ደረጃ ማቅረብ ግዙፍ ስራ መሆኑ መካድ የለበትም$ ይሄው ግዙፍ ፕሮጀክት በሂደት በርካታ ኮንትራክተሮች ባለሞያዎች በዚሁ ዙርያ የተደራጁ የስራ ማህበሮች በመፍጠር ረገድ ግዙፍ ሚና ተጫውቷል$

ለድሀው እና መካከለኛ ገቢ ላለው የህብረተሰብ ክፍል ያስገኘውም ውጤት የምር የሚያበረታታ ነው$ እነዚህን ስኬቶቹን ማንሳት በሂደቱ ያጋጠሙ እጥረቶችን መካድ ተደርጎ መታየት የለበትም$ የጥራት የመጓተት የእጣ እና ቤት ያላቸውን ሰዎች ከሌላቸው መለየት አለመቻሉ በዚህ ረገድ የሚታዩ መፍትሄ የሚሹ ጉዳዮች ናቸው ብሎ ማንሳትም ይቻላል$

በመሆኑም እድገቱ ሲጀመር ሁሉንም ችግሮች ያስወግዳል ተብሎ የሚገመት ባይሆንም እንደዚያ መገመቱም ስህተት ቢሆንም እድገቱ ግን በርግጥም ዘላቂ የሀገሪቱን ጥቅም ሊያስጠብቅ በሚችልበትና ድህነትን ሊቀረፍ በሚችልበት አግባብ እየተከናወነ ስለመሆኑ መካካድ ተገቢ አይሆንም$

የድህነት ቅነሳ
ኢትዮዽያ ከዛሬ አስር አመት በፊት 38 ነጥብ 8 በመቶ የሚሆኑ ከድህነት ወለል በታች ያሉ ዜጎች ነበሯት$ ባለፉት ዘጠኝና አስር አመታት በገንዘብና ኢኮኖሚ ሚንስትርም ይሁን በአለም ባንክ ሪፖርት መሰረት ሀገራችን የ9 ነጥብ 1 በመቶ የድህነት ቅነሳ ማድረግ ችላለች$ ይሄ ማለት ወደ 2 ነጥብ 5 ሚሊየን የሚጠጋ ቁጥር ያለው ሰው በእድገቱ ከድህነት ወለል በላይ ሆኗል$ እንደ መረጃዎቹ ሀገራችን የዋጋ ግሽበትን ባለ አንድ ዲጂት አድርጋ ተጉዛ ቢሆን ኖሮ ከድህነት የሚወጣው ህዝብ ቁጥር ከዚህም የላቀ መሆን ይችል ነበር$

ከዚሁ ጋር አያይዘን ብናየው ጥሩ የሚሆነው ከእጅ ወደአፍ በሆነ መልኩ የሚኖረው አርሶ አደር በተለይም ድርቅ በተደጋጋሚ በሚያጠቃቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎች በአመዛኙ ሁኔታው ወደ ርሀብ የሚቀየርበት ሁኔታ የነበረ መሆኑ ይታወቃል$ እንደ ቦረና እና ሶማሊያ አካባቢ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የሚሰሩት ትላልቅ ግድቦች እንደተጠበቁ ሆኖ በተለያዩ አካባቢዎች የሚፈጠሩ ድርቆችን ተከትሎ የሚከሰተውን የምግብ እህል እጥረት መንግስት በአስተማማኝ ሁኔታ ለመፍታት የሚጠቀምበት የአደጋ ቅድመ ማስጠንቀቂያና ሲከሰትም ችግሩን ለመቅረፍ የሚጠቀመው መንገድ ከእህል ክምችቱና የጥምረት ስራው ጭምር ስኬታማ በመሆኑ በሌሎች ተመሳሳይ ችግሩ ባለባቸው የምስራቅ አፍሪካና ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ለመተግበር ልምድ እየተቀመረ መሆኑን አውቃለሁ$

መረጃዎቹን ከአውሮፓ ህብረት የፓርላማ አባላት የዚህ አመት ጉብኝትና ከቅርብ ግዜው የምስራቅ አፍሪካ ከፍተኛ የርሀብ አደጋ ወቀት ኢትዮዽያ የነበራት የተሻለ አፈጻጸም በተለያዩ አለማቀፍ የእርዳታ ድርጅቶችና በአውሮፓ ህብረት ተደናቂነት ያገኘ መሆኑን ማስታወስ ይቻላል$ ይሄ በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ዜጎቻችን መሰደድ ምክንያት የነበረን ችግር በዚህ መልኩ ማንም ከአካባቢው ሳይፈናቀል ድርቁ ወደ ርሀብነት እንዳይሸጋገር ማድረግና ከራሳችን መጋዘን አውጥተን መመገብ መቻል ትልቅ ስኬት ነው$ በርግጥ የአለም አቀፉ ማህበረሰብ ድጋፍ በዚህ ረገድም ቢሆን ግዙፍ መሆኑ ባይካድም$ ምክንያቱም ከመጋዘን ያወጣነውን ምግብ የሚተካ እስከ ስድስት ወር ተጓጉዞ የሚደረስ የምግብ እህል እርዳታ ይሰጡናልና$

ርሀብን በዚህ መልኩ መቆጣጠር መቻልና አርአያ ተደርጎ ሊታይ በሚችልበት ገጽታው መምራት የእድገታችን ማሳያና በግብርና ሚኒስቴር በኩል የሚሰራው የአደጋ መከላከልና ዝግጁነት ስራ ሁነኛ ለውጥ እያሳየ ስለመሆኑ አያጠራጥርም$