Tuesday, September 3, 2013

ኢትዮጵያ እንዳትገነጣጠል- ክፍል ሁለት




ክፍል አንድ ካነሳናቸው ጉዳዩች የሚለጥቁ ራስን ማስተዳደር እንደ መለያያ ስትራቴጂ 1983 ሀገራችን የሚሉና ሌሎች ጉዳዩችን የሚዳስሰው የጹሁፉን ሁለተኛ ክፍል እነሆ

መብት እንደ ጥርጣሬ መፍጠርያ

አንዳንዶች ራስን በራስ የማስተዳደር መብት የተከበረው ይሆነኝ ተብሎ ህዝቦችን ለማንኳሰስና በመሀላቸው ጥርጣሬ ለመፍጠር ነው የሚል ክስ ያቀርባሉ፡፡ አለመተማመኑን ኢህአዴግ የሚፈልገው ወጥና ጠንካራ ተቃውሞ እንዳይገጥመው ነው በሚል ክሱን ያጠናክራሉ፡፡ ይህ ደግሞ እድሜውን ለማራዘም ያገለግለዋል ብለው ያምናሉ፡፡


አንደኛ በተፈጥሮአዊ ባህሪያቸው እነዚህ ህገመንግስታዊ ድንጋጌዎች እንዴት ነው አለመተማመን የሚፈጥሩት ብሎ መጠየቅን ያሻል፡፡ በየክልሉ ያሉ የተለያዩ ብሔሮች ሰሜኖች እየመሩን የሚኖሩት እኛ ራሳችንን ማስተዳደር ተስኖን ነው ወይ በሚል ቁጭት የሚንገፈገፉበትን ጉዳይ ነው የመለስው፡፡ በርግጥም ትክክል ናችሁ አዎ ራሳችሁን ማስተዳደር ትችላላችሁ ሰሜኖቹም የማስተዳደር ስራውን ለናንተ እንዲያስረክቡ ህገመንግስቱ በሚጠይቀው መሰረት ተደርጓል ነው የሚለው፡፡ ሰሜኖቹም የማስተዳደር ተፈጥሯዊ አቅምና መብት አላቸው አካባቢያቸውን በዚያው መሰረት ያስተዳድራሉ የሚል ፍትሀዊ ድንጋጌ ነው፡፡


ይሄ በርግጥም የመብቶችን በተሟላ መንገድ መከበር ይገልጻል እንጂ በምን ሚዛን ነው ጥርጣሬ በህዝቦች መካከል የሚያነግሰው፡፡ በመላው ሀገሪቱ ፍትሀዊ ነው ተብሎ ሊወስድ ቢችል እንጂ በምንም ሚዛን መጠላላት እና ጥርጣሬ የሚከስት ሆና አላገኘውም፡፡ በባህሪው ያን የማድረግ አቅም የለውም፡፡


ይልቅ ለአካባቢው ማህበረስብ የማስተዳደር ሀላፊነቱ ሲመለስ ከዚያ ቀድሞ በነበረው ግዜ በአመራር ቦታው ላይ የነበሩ ሰዎች የመሪነቱን ቦታ ሲያጡ አብሮ የሚደርቅ እና የምረዳው የሚያጡት ጥቅም ይኖር ይሆናል፡፡ ያ በቤተሰብ እና በግለሰቦች አንጻር ሲመዘን ጉዳት እንዳለሁ እረዳለሁ፡፡ ግን ድንጋጌው ከሚያስገኘው ጥቅም አንጻር እና ነጻነት ከሚያጎናጽፋቸው መላው የኢትዮጵያ ብሄሮች አኳያ ሲመዘን እዚህ ግባ የሚባል ጉዳይ አደለም፡፡ የለውጡም አላማ ይህን የመሰሉ ግለሰቦች ጥቅም ማሳጣት ሳይሆን ራሱን የመምራት ተፈጥሮአዊ ብቃት ያለውን ህዝብና ዜጋ መብት ማክብርና ማስከበር ነው፡፡


በዚህ ሂደት አማራው የተጎዳ በማስመሰል ለማቅረብ የሚሞከርበት አዝማሚያ ሌላው ነው፡፡ በጋሞ ጎፋ አርባምንጭ ተወልዶ እንዳደገ አማራ የሆነውን አውቀዋለሁ፡፡ በአመዛኙ ከሰሜን እና ከሸዋ በመጡ ሰዎች የተያዘው የሀላፊነት እና የመሪነት ቦታ በአካባቢው ተወላጆች ተወስዷል፡፡ ያ ግን በዋናነት የሚያሳየው የአካባቢው ሰው የስልጣን ባለቤት መሆኑን እንጂ ይሆነኝ ተብሎ በቀድሞዎቹ መሪዎች እና ዜጎች ላይ የደረሰን በደል አደለም፡፡


አማራውም ትግሬውም ሸዌውም በአካባቢው ራሱን የመምራት መብት እንደ ተጎናጸፈ ኁሉ ሌላውም ብሄር ራሱን የመምራት ሀላፊነትን እንደ መብትነቱ መጎናጸፉ ምንም ክፋት የለውም ብቻ ሳይሆን ተገቢና ትክክል ነው፡፡ ምን ያክል እርካታም በጋሞጎፋ ተወላጆች ዘንድ እንደፈጠረ አውቃለሁ፡፡


መተቸት ያለበት እንዲህ ያለውን ራስን የመምራት ሃላፊነት በአካባቢው በሚኖሩ ሌሎች ብሄሮች ተወላጆች ላይ ጉዳት እና አድሎ ለማድረስ የሚጠቀሙበት ሀላፊዎች እና ሌሎች የአካባቢው ተወላጆች የሚኖሩ ከሆነ ነው፡፡ እንዲህ አይነት ሰዎች እንዳይኖሩ ማድረግ የሚቻል ባይመስለኝም እንዲህ አይነት ጠባብ አመለካከታቸውን ሲተገብሩት ያለርህራሄ ማድረቅ ግን ያስፈልጋል፡፡

ኢትዮጵያ እንዳትገነጣጠል- ክፍል አንድ


ባለፈው ግዜ ከነጃወር የተንሸዋረረ የማንነት እና የዜግነት ጥያቄ በመነሳት እቺ አገር ያለችበትን ሁኔታ የሚዳስስ ጽሁፍ ለማቅረብ ቃል ገብቼ ነበር፡፡ በዚያው መሰረት ሀገራችን ሳትገነጣጠል ልትቆይ የሚያስችላትን አማራጭ በኔ እይታ አቅርቤዋለሁ፡ እንምከርበት እንሟገት፡፡

እንደ መግቢያ
በጥሬው ኢትዮጵያ እንዳትገነጣጠል ማሰብና በአንድነት አጽንቶ በእድገት አልቆ ሊያስቀጥል የሚችል ስርአትና አመራር መፍጠር የተለያዩ ናቸው፡፡ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ አንድነቱን የሚመርጠው መሆኑ አነጋጋሪ አደለም፡፡ አንድነት ተጠብቆ ሊዘልቅ የሚችልበትን አማራጭ በመምረጥ ረገድ ግን ልዩነቶች ይስተዋላሉ፡፡


በወሳኝነት በፖለቲካው መድረክ ከዚህ አኳያ የሚፋለሙት አስተሳሰቦች ሁለት ናቸው፡፡ አንዱ ኢህአዴግ ያቀረበው ራስን በራስ የማስተዳደር እስከ መገንጠል አማራጭ ሲሆን ሌላኛው የተወሰኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያቀነቅኑት በብሄር ሳይሆን በጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ እንዲተዳደሩ የሚለው አማራጭ ነው፡፡ ይህ አማራጭ ከክልሎቹ መዋቅር እስከ ፌደራል መንግስት መዋቅር ባህርያት ድረስ ቁርጥ ያሉ አማራጮች ያበጀ አይመስልም፡፡ በግርድፉ የሚያቀርበውን ሀሳብ ግን እንየው፡፡


ጂኦግራፊያዊ የፌደራል ስርአት አማራጭ
እንደ ኢዴፓ ያሉ ይህን አማራጭ የሚያቀርቡ ፓርቲዎች ህዝብ ብሄራዊ ማንነቱ ከግምት ሳይገባ እንደ አቀማመጡ አመቺነት ወሎ ጎጃም ሲዳማ ሀረርጌ አይነት ብለን  እንደ አመቺነቱ እናስተዳድር የሚል አማራጭ አይነት ነው የሚያቀርቡት፡፡ አማራጩ በርግጥ ጥርት ባለ መልኩ ተብራርቶ ባይቀርብም እነ ልደቱን ከመሳሰሉ ፓለቲከኞች ከሰማሁት ገለጻ ተነስቼ ስናገር በጂኦግራፊ ተከፍሎ ሲያበቃ የብሄሮችን በገዛ ቋንቋቸው የመጠቀም መብት ግን ያከበራል ይላሉ፡፡


በተጨማሪም የመሪዎች ምርጫ በህዝቡ የሚካሄድ ስለሚሆን በጂኦግራፊ መከፈሉ ችግር አያመጣም ይላሉ፡፡ ይሁንና ይህ አይነቱ ውሳኔ እንደ ኦሮምያ ሶማሊያና አፋር ለመሳሰሉ በርካታ ሌሎች ብሄሮች አርኪ መልስ አይመስልም፡፡ ምክንያቱም ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር ጥያቄ ዋናው የማንነት እና የእኩልነት ጥያቄ ነውና፡፡ ይህ አማራጭ አጀንዳውን ተራ የፌደራል ስርአት የመመስረት እንጂ ከማንነት ራስን ከማስተዳደርና ከእኩልነት አንጻር ከሚነሱ ጥያቄዎች ጋር በማስተሳሰር ያጤነው አይመስልም፡፡


እንዲያውም ይህ አይነቱ አተያይ በጠባብ ከባቢያዊ አስተሳሰብ ድጋፍ ለሚሰበስቡ ፓለቲከኞች የሚያበረታታ አጀንዳ የሚፈጥርላቸው ይመስላል፡፡ የመገንጠል አጀንዳ የሚያቀነቅኑትም ዛሬም ቢሆን ራስህን ማስተዳደር ያልተፈቀደለህ ስለማትታመን ነው ዛሬም መብትህ አልተከበረም በሚል ዝማሬ ለማነሳሳት ይጠቀሙበታል፡፡ በጣም ቢዳከሙም ዛሬም መሰል የመገንጠል አስተሳሰቦች የራስ አስተዳደር በተከበረበትም ሲራመዱ የምንታዘበው ይህን የህዝቡን ፍላጎት ጠምዞ ለአጀንዳቸው ለማዋል ታስቦ መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡

መፍትሄ ፈብራኪ ወይስ ወቀሳ ጠማቂ


ነጻ የወጣ ህሊናና ህዝብ አብይ ተግባር ኢኮኖሚያቸውን መቀየር ነው፡፡ ዲትሮይቶቹን እና ሲሊካን ቫሊዎቻቸውን ማነጽ፡፡ ነጻነታቸው ከሚያስጀምሯቸው ሁነኛ ጉዳዮች መካከል ዋነኞቹ ኢኮኖሚያዊ ናቸው፡፡ የፖለቲካ ነጻነትም አብይ ፋይዳ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ማስገኘት መቻሉ ነው፡፡ የህዝብ አብይ ጥያቄዎች ዞሮ ዞሮ ኢኮኖሚያዊ ናቸውና በተለይ እንደኛ ባለ ደሀ ሀገር፡፡ የፖለቲካ ጥያቄዎችም አብይ ፋይዳ ኢኮኖሚያዊ ነጻነቶችን ማረጋገጥ መቻል መሆኑ ይታወቃል፡፡


ኢኮኖሚውን ማንደርደር ወይስ ፓለቲካውን ማንተክተክ
በብዙ መልኩ ሲመዘን የኛ ሀገር ፖለቲካ ያለበት ደረጃ ኢኮኖሚያዊ ጉዳዩችን ወደፊት በመግፋት ላይ የሚያተኩር ሳይሆን በመብት ላይ የተንጠለጠለ ከመብትም ደግሞ በተሟላ መንገድ ያሉ ጭብጦች ላይ ሳይሆን በየወቅቱ ከሚወጡ ደንቦችና ህጎች ውስጥ በተወሰኑ ለወቀሳ ያመቻሉ በሚባሉ በወጉ ባልተላመጡ ጉዳዩች ላይ ተንተርሶ ገዢውን ፓርቲ ለማጣጣል ከመሞከር ባለፈ በሀራችን የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች ፕሮግራሞቻቸውን በወጉ በተጠኑ ሀገራዊ ጉዳዩች ዙርያ የማያደራጁ በየወቅቱ በሚኖሩ ክርክሮች ላይ ራሳቸውን ከማስተዋወቅ ይልቅ በድክመትም ቢሆን እያነሱ ሲያስተዋውቁ የሚውሉት ኢህአዴግን  የሆነብት ሁኔታ ነው ያለው፡፡


በዚህ ሂደት የፖለቲካውን ሙቀት ከመጨመር በዘለለ ምናልባትም በተወሰኑ ጉዳዩች ላይ ገዢውን ፓርቲ ከማብጠልጠል ባለፈ በሀገሪቱ ወሳኝ ስለሆነው የኢኮኖሚ እድገት ወዴትነት እንዴትነት በምን አማራጭ ሊያድግ እንደሚችል በማመላከት ረገድ እዚህ ግባ የሚባል ግብአት እስከማይኖራቸው ደርሰዋል፡፡


በዚህ የተነሳ በኢኮኖሚው ላይ ፓርቲዎቹ የሚሰጡት ትንታኔ ግለሰቦች ከሚሰጡት የአሉባልታ ትንታኔ የተሻለ ብስለት የማይታይበት እና ወትሮም ገዢው ፓርቲ እያሳደገው ያለውን ኢኮኖሚ እንዴት በላቀ የእድገት ምጣኔ እንደሚያሳድጉት ሊያመላክቱን ቀርቶ አሁን ባለውም ቁመናው እንዴት እንደተደራጀ ምን ለውጥ እያስገኘና ምን እጥረቶች እየፈተኑት እንዳሉ እንኳ በወጉ የማይገነዘቡ ፓርቲዎች የተጠራቀሙበት ምህዳር በመሆን ቀጥሏል፡፡


ይሄ የሆነው እና እየሆነ የቀጠለው ተቃዋሚዎቹ ወደ ፖለቲካው ጎራ ከተፍ የሚሉት አንድም በፖለቲካ ፓርቲ መሰባሰብ ያስገኛል የሚሉትን ጥቅም ለመቀራመት በሌላም ይህ ካልሆነ ደግሞ ኢህአዴግን በሚረባም በማይረባም ጉዳይ ስለሚጠሉት ብቻ ይሆንና ተቃውሞ የጥላቻ መልእክት ከመቀመር እና አቤቱታ ከመዘመር የተሻለ ቁምነገር የሌለው ሆኖ ያርፋል፡፡ ለዚህ ነው የሀገራችን የተቃዉሞ ፖለቲካ ከአቤቱታ ከፍ የሚል ሚና መጫወት የተሳነው፡፡

እዚህ አገር ብዙ ችግር አለ




አዎ እዚህ አገር ችግር አለ፡፡ ችግሩን ደግሞ በየእለቱ በየሰአቱ በየደቂቃው እየኖርነው ነው፡፡ በአንድ በኩል የመሰረተ ልማት እጦቱ መሰረተ ልማቱ ሲኖርም በአግባቡ አለመስራቱ የሚፈጥርብንን ምሬትና ጉዳት በሌላ በኩል በየለቱ የሚሞቱት ሕጻናት እና እናቶች በየግዜው መመገብ ያልቻልናቸው ነገሮችና ልናገኝ ያልቻልነው የህክምና አገልግሎት የበለጠ ያሳምመናል በቀላሉ፡፡ ልናገኝ ስንችል ያላገኘነው መንግስታዊም ግለሰባዊም አገልግሎት ይጎዳናል ያስመርረናልም፡፡


ቁምነገሩ ግን እንደማንኛውም አንድ ግለሰብ ማማረርና የችግር አለ ትርክት ማሳመርና ማስዋብ አደለም፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና በፖለቲካውና በኢኮኖሚው በንቃት የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች ሁነኛ ሀላፊነት የችግሩን ምንጭ በአስተማማኝ ጥናት መለየት ምንጮቻቸው ለታወቁ ችግሮች ተገማች እና ሳይንሳዊ መፍትሄ መቀመር እና ይሄው መፍትሄ ተተግብሮ እሚፈለገው ለውጥ እንዲገኝ ማድረግ ነው፡፡


ከመደበኛው ማህበረሰብ እኩል ችግር አለ እያሉ ለማስተጋባት ከሆነ በፓርቲ ደረጃ የምንሰባሰበው ይሄ ፋይዳ የለውም፡፡ መሰባሰብ እንደ ፓርቲ መቆም የፖለቲካ አጀንዳ ነድፎ መንቀሳቀስ ጠቃሚ የሚሆነው መደበኛው ግለሰብ አጥንቶ ሊደርስባቸው የማይችላቸውን ጉዳዩች በተደራጀ መልኩ አከናውኖ ችግሮች የሚፈቱበትን አግባብ የሚቀመር ከሆነ እንጂ ከመደበኛው ግለሰብ እኩል ችግር አለ ለማለትማ በፓርቲ ደረጃ መሰባሰብ አያስፈልግም፡፡ ያንማ ሰለማዊ ሰለፈኛም ያደርገዋል፡፡ ቁምነገሩ መፍትሄውን አፈላልጎ ማግኘት በዚያ ዙርያ ድጋፍ አሰባበስቦ ሕዝብን አሳምኖ ምርጫ ማሸነፍና የመሪነቱን ሚና ተቀብሎ ሕዝብ ይገባዋል የምንለውን ጥቅም ማሳካት መቻል ነው፡፡


በምን ስሌት ነው ችግር አለ ብሎ የምናውቀውን ችግር ስለተረከልን አንድን የፖለቲካ ድርጅት ሀገር የመምራት ሀላፊነት የምንሰጠው፡፡ ጥያቄው የመፍትሄ እንጂ የችግሮች መኖርን ክሽን ባለ ቋንቋ የማቅረብ ያለማቅረብ ጉዳይ አደለም፡፡ ችግር እንዳለ ኑሯችንን ጠቅሰው አስረዱን እንበል ይሄን ማድረጋቸው የሚባለውን ችግር የመፍታት ሁነኛ መነሻውን የመለየት እና የተበጀውን መፍትሄ የመተግበርና የማስተግበር ድርጅታዊ አቅማቸውንና አቋማቸውን ሊያሰየን ይችላል እንዴ? አይችልም፡፡ የፓርቲ ሁነኛ አላማም ህዝብ የሚማረርበትን ችግርና አሁን ካለው ቁመና አንጻር ወደፊት ሊገጥሙት የሚችሉትን ተገማች ተግዳሮቶች በመተለም ችግር የሚፈታና ሀብት መፍጠር የሚችል አመራር መስጠትና ማስተግብር እንጂ ችግር ተራኪ ድምጽ መሆን አደለም፡፡

የፖለቲካ ሀላፊነት እንደ ችግር መፍቻ ቃልኪዳን




አንድ የፖለቲካ ፓርቲ ለህዝብና ለደጋፊዎቹ የሚገባው ቃልኪዳን ለውጥ ነው፡፡ በተገማች እና በሳይንሳዊ ዘዴዎች መመላከት ማሳመን ማነሳሳት የሚችሉ የለውጥ ቃልኪዳኖች፡፡ እንዲህ ያለ ቃልኪዳን መግባት ደግሞ አላማ ይጠይቃል፡፡ ሀገር የመለወጥ አላማ፡፡ ሀገር ለመለወጥ የተነሳሳ በዚያው አላማ ዙርያ መሸ ጠባ ሊተጋ ይገባል፡፡ ይህን በመሰለ አላማ ዙርያ የማይሰራ ያን ማሳካት የሚችሉ ጥቅል ፍልስፍናዎች ከዚያ የሚቀዱ የረጅም ግዜ የመካከለኛና የአጭር ግዜ እቅዶች ነድፎ በነዚያ ዙርያ ህዝቡ ግንዛቤ እንዲኖረው የማይተጋ ፓርቲ የሚቀረው መንጠልጠያ ትችት ብቻ ነው፡፡ ትችት ጌጡ ሆኖ የሚያርፈው እንዲህ አይነት ትልም የሌለው ፓርቲ ነው፡፡


ይሄን መሰሉ የፓርቲ ቁመና የጠራ አላማ እና ከአላማ ለአፍታም ቢሆን አይንን አለመንቀል ይጠይቃል፡፡ እንዲህ ባለ ትኩረት የሚሰራ ቡድን በርካታ የሚያቅዳቸው የሚያነሳ የሚጥላቸው ጉዳዩች ስለሚኖሩት ስለራሱ በማውራት የራሱን ፕሮግራም በማነጻጸር ይጠመዳል፡፡ የሌሎቹን ተፎካካሪ ፓርቲዎችም አማራጮች አዋጭ አለመሆን የሚያነሳው አማራጩን ሲያስተጋባ በማሳያነት ወይም በማነጻጸሪያነት ሲያነሳው እንጂ ነጋ ጠባ ስለባላንጣው ሲያወራ የሚከርምበት ሁኔታ ሊኖር አይችልም፡፡


ስለ ባላንጣቸው በማውራት የሚጠመዱ ፓርቲዎች ዋነኛ ችግር ስለባላንጣቸው ያላቸው የከፋ ጥላቻ አደለም፡፡ ትልቁ ችግር ለሀገራቸው የሚያቀርቡት አማራጭ ራእይ የሌላቸው መሆኑ ነው፡፡ አጀንዳ ያለው ቡድን ስለሌሎች ለማውራት ግዜ አይኖረውም፡፡ በሚያገኛት የተወሰነች የሚዲያ አጋጣሚ የፓርቲዉን መልእክት በማስተላለፍ ስራ ላይ ብቻ ይጠመዳል፡፡ በተቃራኒው ላይ የሚያተኩር ቡድን ውድቀት እንደ ፓርቲ የሚታገልበት ጥርት ያለ አላማ እና የተተነተነ እቅድ አለመኖር ነው፡፡

Saturday, August 31, 2013

#Wahabi/Salafi trends in Ethiopia # its Tactics

They preach the radical wahabi/salafi doctrine to prepare the ground for radicalism in Ethiopia

When the government tell them to stop their radicalization and take the right route, they accuse the government for preaching Ahbash, another moderate sect like Sufi Islam, which is the form of Islam, Muslims practice in the country for so long

They try and snatch the leadership by force in mosques to effectively plot their radical agenda all over the country; when they are told to work with in the rule of the land and peacefully
they simply turn and accuse the government for interfering in their religion as if they are religious and as if they represent the millions of Muslims across the country.

Wednesday, August 28, 2013

እውን ኤርትራን ማን አንገት አደረጋት?

ኤርትራ ክብር የሚገባቸው ሕዝቦች መኖሪያ መሆኗ እንደተጠበቀ ሆኖ የራሷን ጉዳይ በራሷ መወሰን ያለባት ሀገር መሆኗ እንደተጠበቀ ሆኖ ሲያበቃ አንገት የሚያደርጋት ቁመና ያላት ግን አደለችም፡፡ ወደብም ኤርትራን አንገት አያደርጋትም፡፡ ምናልባት አንገት ትሆን የነበረው ኢትዮጵያውያን ከአሰብ ወደብ ብቻ ተቆፍሮ በሚወጣ ተአምረኛ ቁሳቁስ የምንኖር ቢሆን ነበር፡፡ 

ካልሆነ ግን ወደብ በሚታወቀው የገቢና የወጪ እቃ ማስተላለፊያነቱ ከተመዘነ ኤርትራ በማንኛውም ሚዛን አንገት አደለችም፡፡ ልትሆንም አትችልም፡፡
 
እንዲያውም ከሸቀጥ አንጻር ከታየ አንገት መባል የነበረባት ወደብ አልባዋ ኢትዩጵያ ናት፡፡ ኤርትራ በማታመርታቸው ጥሬ እቃዎች ጥሩ ላኪ አገር ሆና የነበረውም ከጦርነቱ በፊት ይህን ሀብታችንን ከኛ ገዝታ በመውሰድ ታቀርብ የነበረ በመሆኑ  እንደሆነ መረሳት የለበትም፡፡ ጉዳዩ ከህዝቦች መብት አንጻር መታየቱ ከቀረ በሚል ያመጣሁት ንጽጽር እንጂ የሁለቱ ህዝቦች ጉዳይ ከሀብት አንጻር መመዘን አለበት ብዬ አላምንም፡፡
 
ወደቡን ስላጣነው ማጣጣል አለብን ብዬም አላምንም፡፡ ወደብ ራሱን የቻለ አስፈላጊነት እንዳለው አልዘነጋም፡፡ ለወደብ ሲባል ግን ወጣቱ እየታፈሰ ለጦርነት ሲማገድ መክረም አለበት የሚል ደካማ አማራጭም አልወስድም፡፡ ወደብ ዛሬ ባለው ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ሲመዘን የሚኖረው ተጽእኖ ወደብ ወይም ሞት የሚያሰኝ አደለም፡፡
 
በተለያዩ ግዜያት ወደብ አልባ በሆኑ አስራ ስድስት የአፍሪካና 31 አለማቀፍ ደሀ አገሮች ላይ የተደረገ ጥናት እንደሚያመላክተው ወደብ አልባ አገሮች ወደብ ካላቸው አገሮች ጋር ሲነጻጸር ከትራንስፓርት እና ተያያዥ ወጪዎች አኳያ 50 በመቶ ከፍ ያለ ወጪ ለማውጣት ይዳረጋሉ፡፡

አንዳንድ ጥናቶችም ወደብ አልባ አገሮች ወደብ አልባ በመሆናቸው ብቻ አመታዊ ኢኮኖሚያ እድገታቸወ 0.5 በመቶ ድረስ የእድገት ምጣኔ ቅናሽ እንደሚያሳዩ ይጠቁማሉ፡፡ ይህ ግን በደሀ ወደብ አልባ አገሮች ሁኔታ አኳያ እንጂ ወደብ አልባነት ከዚህ ጋር የግድ የሚያቆራኝ ሆኖ አደለም፡፡

አንደኛ እነዚህ ደሀ ወደብ አልባ ሀገራት በደሀ ባለወደብ ሀገራት አጎራባችነት ያሉ በመሆኑ ያልዳበረ መጓጓዣ እና ትራዚት አገልግሎት ስላላቸው ወደብ አልባውንም አገር ራሳቸውንም በከፍተኛ ደረጃ ተጠቃሚ ማድረግ በሚያስችል ቁመና ላይ የማይገኙ በመሆኑ ነው፡፡  

ወደብ አልባ ሆነው ሲያበቁ የርስ በርሱ ንግድ ልውውጥ በተጠናከረበት እና የትራንስፓርት ዘርፉ ባደገበት አካባቢ ያሉ እንደ ኦስትርያ ስዊዘርላንድ እና ቤልጂየም ያሉ አገሮች ምን ያክል መልማት እና የበለጸጉ ሀገሮች መሆን እንደቻሉ የምንታዘበው ነው፡፡
እነዚህ አገሮች ሸቀጥ ለማስገባት የግድ ወደባህር በር የማያዩበት ከበለጸጉት ጎረቤቶቻቸው የሚገበያዩበት የወጪ ንግዳቸውንም ወደብ በወሳኝነት ሳያስፈልግ ለጎረቤቶቻቸው የሚያቀርቡበት ሁኔታ ስላለ ለኛ ወጥመድ የሆኑ ሁኔታዎች ለነሱ እምብዛም ቁምነገራቸው ያልሆነበት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ 

የኛ ከባቢያዊ ሁኔታ ከዚህ አኳያ ያለውን በጎ ያልሆነ ተጽእኖ እንገነዘባለን፡፡ ለዚያ ነው ኢህአዴግ ጎረቤቶቻችን እንደ አቅም እንጂ እንደ ጠላት የማይፈርጀው፡፡ የሱማሌ የሱዳንና ሌሎች ከባቢያዊ ሁኔታዎችንና አህጉራዊ ሁኔታዎችን በትኩረት ኢህአዴግ የሚተጋባቸው የአህጉሪቱ ማደግ የኢትዩጵያ ማደግ የከባቢው መለወጥ የኢትዩጵያ ለውጥ መሆኑን በመረዳት ነው፡፡

በመሆኑም ከነዚ መነሻዎች ተነስተን ስንቃኝ ኤርትራ ለኢትዮጵያ አንገት የምትሆንበት ቤሳቢስቲን ተጨባጭ ማስረጃ የለም፡፡ ለኔ ወጣትን ለጦርነት ሲማግዱ ከመኖር የግድ የሚል ከሆነ 0.5 አመታዊ የእድገት ምጣኔያችንን ቀርቶብን በሰላም መኖራችን ሁነኛውም መለኛውም አማራጭ ነው፡፡ ይሄ ማለት ኢትዩጵያና ኤርትራ አንድ ሊሆኑ የሚችሉበት እድል ካለ ባፍጢሙ ይደፋ ማለት አደለም፡፡ ግን የሚሆነው በመግባባት እና በመተማመን ነው፡፡ በአንገትና በበድን የሰከረ አተያይ የሚመራ ፖለቲካ ለዚህ መሰሉ ስክነት የታደለ አደለም፡፡

ኢህአዴግ በለጋ እድሜው ይህን አማራጭ ተረድቶ ማቅረብና ማስተግበሩም በለጋ እድሜው የፈጸመው ሁሌም የሚታወስ በሳል እና ትልቅ አበርክቶው እንደሚሆን አምናለሁ፡፡ ከወንበሬ ብድግ ብዬ ለዚያኔዎቹ ወጣቶች ለአሁኖቹ ጎልማሶች አድናቆቴን እገልጻለኁ፡፡ በርግጥም ኤርትራ አንገት አልነበረችም ዛሬም ወደፊትም አንገታችን አትሆንም፡፡  

አሰብም እንደ ወደብ እንደ ወርቅ እየተቆረጠ የሚሸጥ ጸጋ አደለም፡፡ አገልግሎት ሲሰጥ ብቻ ነው ሀብት የሚሆነው፡፡ አገልግሎት ሊሰጥ የሚችለው ደግሞ ለኛ ብቻ ነው፡፡ እኛ ስንጠቀመው ለኤርትራውያኑ ግዙፍ ገቢ ይሆናል ትንሽ ቁጥር ያለው ህዝብ ከመሆናቸው አንጻር ትልቋ አገር የሚኖራት ትልቅ የወጪና የገቢ ንግድ የሚያስገኘው ዳጎስ ያለ ገቢ ስለሚኖር፡፡ እንዲያውም ኤርትራ በአካባቢው ተመሳሳዩን አገልግሎት ሊያቀርቡ የሚችሉ በርካታ ሀገሮች መኖራቸውን ተረድታ የተሻለ አገልግሎት ለመስጥትና ተመራጭ ወደብ ለመሆን ተፍ ተፍ ማለት ነበረባት፡፡
 
ለአንድ አገር አንገት የሚሆን ሚና ሊሆን የሚችለው የራሱ መንግስት የአመራር ሚናና የህዝቡ ተነሳሽነት ብቻ ነው፡፡ በመሆኑም ነው የአንገትነት ታፔላ የተለጠፈላት ሀገርም ከሄደች በኋላ እቺ አገር በአለም አቀፍ ደረጃ ፈጣን እድገት ከሚያስመዘግቡት ቻይናና ሕንድ ተርታ መግባት የቻለችው፡፡ አንገታችን ወዴት ነሽ ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ 

አንገታችን ልማታዊ ስራዎቻችን ላይ ያነጣጠረ ትጉህ መንግስት ትጉህ ፓርቲና ትጉህ ህዝብ እንጂ ኖረንም ቀረም ወደብ አደለም፡፡ ወደብ ቢኖረው እሚጠላ የለም ኖረም ቀረም ግን የህዝቡን እና የመሪ ድርጅቶችን አይተኬ ሚና ለወደብ በመስጠት ራሳችንን አሳንሰን ልናይ አንችልም፡፡ ብናደርገውም ስህተት ከመሆን ያለፈ ፋይዳ የለውም፡፡

ኤርትራ በኤርትራውያን ውሳኔ አንድ ሆና ብትኖር የሚጠላ ያለ አይመሰለኝም፡፡ ቢሆን ደስተኛ ከሚሆኑት መካከል ኢህአዴግ አንዱ አንደሚሆን አምናለሁ፡፡ አንገት በሚል መንፈስ ግን አደለም፡፡ አንድ ሆኖ ለረጅም ግዜ እንደኖረ ህዝብና አብሮ መኖሩ ለሁለቱም ህዝቦች የሚያስገኘው ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጥንካሬ ስለሚኖረው ነው፡፡

ሁኔታ እንዳይፈጠር የተበላሸ ሚና የነበረው ደግሞ ዛሬም ትላንትም ኤርትራን እንደ አንገት የሚያየው የተቃውሞ ቡድን ነው፡፡ በዚህ በሰከረ ተመሳሳይ ስሌት ሲነዳ የነበረው ሻብያ ወደቡ የግመል ማጠጫ ከመሆን በዘለለ ፋይዳ እንደሌለው በተግባር ሲረዳ ደግሞ የገባበት አዘቅት አካባቢውን በማተራመስ ኢትዮጵያን የኤርትራ ብቻ ደምበኛ አድርጎ የማቆየት አዝማሚያ ነው፡፡ በሶማሌ ያሰገባው እጅ ከጂቡቲ ጋር በድንበር ስም ሊፈጥረው የሞከረው ቀውስ በሱዳን በኩል ሊፈጥር የሚሞክረው ቀውስ ተዳምረው ሲታዩ  እውነታውን ትቶ ራሱን እንደ አንገት ሲቆጥር የነበረው ሻብያ ከገጠመው ራሱን አልቆ የማየት ውርደት ለመውጣት የሚደርገውን መፍጨርጨር ነው፡፡  

ኤርትራ የሆነችውን እንጂ ያልሆነችውን ሆና በመታየት በኢትዮጵያ ላይ ልታደርስ የምትችለው ተጽእኖ አይኖርም፡፡ በመሆኑም ኤርትራ አንገት አደለችም ብቻ ሳይሆን ይሄ የወደብ አገልግሎት አቅርቦት ስራዋም በርካታ ተፎካካሪዎች ያሉበት በመሆኑ የተሻለ አገልግሎት በማቅረብ ከፍ ያለ ገቢ ለማግኘተ ቀና ደፋ የሚጠብቃት ሀገር ጭምር ናት ማለት ነው፡፡ በየትኛውም መስፈርት አካባቢውን በማመስ ኢትዮጵያን ለማተራመስ የምትሰራውም ስራ ኢትዮጵያ ልትቆጣጠረው እማትችለው አይሆንም፡፡
 
በመሆኑም አንገት ተብላ የምትቀርበው ኤርትራም አንገት አደለችም ኤርትራን አንደ አንገት የሚያቀርቡልንም ያለኛ ለአገርና አንድነት አሳቢ የለም የሚሉንም ፖለቲከኞችም ለራሳቸው ከሚሰጡት ግምት በተቃራኒ የአገራችንን ፖለቲካና መፍትሄዎቹን በቅጡ ያልተገነዘቡ ናቸው፡፡ አገሪቱ የገጠሟትን ችግሮች በውል ያልተረዱ በመሆኑም መሰረታዊ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል ፖለቲካዊ መፍትሄም ሊያቀርቡ የማይችሉ ሀይሎች ሀገሬ ሀገሬ ስላሉ ብቻ ራሳቸውን ጥሩ ፖለቲከኛ አድርገው ያዩበት እንደሆነ ከዚህ መረዳት ይቻላል፡፡

ይህም መሰሉን የተሳሳተ ግንዛቤያቸውን ባለፉት 20 አመታት በላይ ሊያርሙት ያልቻሉ መሆኑ ደግሞ ከስህተታቸው ለመማር ይቅርና የለም ተሳስተናል ለማለት ያላቸውን ደካማ ስነምግባር የሚያሳይ ነው፡፡ በዚህ ቁመና ሀገር የመምራት ሀላፊነት መረከብ ቀርቶ ለመረከብ ማሰብ በራሱ የሀገሪቱን ህዝቦች ህሊናዊ ብቃትና የምዘና አቅም መናቅ ይመስለኛል፡፡

ወደብን ወሳኝ ጉዳይ አይደለም ብሎ ስለተረዳ ብቻ ሳይሆን ለህዝቦች ውሳኔና ፖለቲካዊ ጥያቄ አክብሮት ስላለው የህዝቦችን ራስ የማስተዳደር እስከ መገንጠል ህገመንግስታዊ ድንጋጌ ያሰጠው ፓርቲ ከዚያ ለጥቆ የጠሩ ፖሊሲዎች በመቅረጽ ሀገር ወደማልማት ስራዎቹ ፊቱን አዙሯል፡፡ በዚያም በቃል ያብራራውን በተግባር አሳክቶ በማሳየት ባለወደቧ ሀገር ያላሳካችውን ወይም ያላሳኩትን የእድገት ምጣኔ ባለፉት አስርት አመታት ደጋግሞ ሀገራችን እንድታሳካ በሳል አመራር በመስጠት ድርብርብ ድል አጣጥሟል፡፡

በመሆኑም የወደብን ሚዛን በአግባቡ ያሰላ ወደብ ያላቸው ዙርያውን ያሉ የአፍሪካ ሀገሮች ያላሳኩትን ባለሁለት አሀዝ እድገት ላለፉት 9 አመታት በተከታታይ ያሳካ ፓርቲና በዚሁ ፓርቲ ዙርያ መተማመን የፈጠረ ሕዝብ የገነባን መሆኑ አኩሪ ሂደት ነው፡፡ ይህን ማሳካት የተቻለው ደግሞ ሁሉም ነገር ወደ ወደብ ወደ ጦርነት ግንባር የሚለው መፈክር በሁሉም ነገር ድህነትንና ኋላቀርነትን ወደ መናድ ግንባር በሚል ቅኝት በመተካቱ ነው፡፡