Monday, December 30, 2013

የአማራው፣ የኦሮሞው እና የትግሬው ዘረኛ ትረካዎች--- ክፍል 2



=======================
በዚህ ትንታኔዬ የኔ የሚባሉትንም ከመተቸት ወደሁዋላ አላልኩም። እውነታውን በጋራ መጋፈጥና በሀቀኝነት ችግሩን ፈተን ሁላችንም በጥረታችን ልክ አሸንፈን እና እኩል ተጠቃሚ ሆነን የምንኖርበት አገር ካልፈጠርን መዘዙ አደገኛ ነው ብዬ ስለማምን የሚመስለኝን ሁሉ ድፍረትና ሚዛናዊነትን አጣጥሜ ላቀርበው ሞክሬያለሁ። መልካም ንባብ።

ስጀምር በኔ አተያይ እንደ ብሄራችን የታሪክ ትረካችን ይለያያል። ታሪኩን እምንዘክርበት ስሜትና ወግም በዚያው ልክ የተለያየ ነው። አንዱን ታሪካችንን ከደማችን እየቀዳን እያነበብን ብዙ አይነት አድርገን ግራ እንጋባለን፣ ግራ እናጋባለን።

ጥቅል ድምዳሜዬን የሚጎሉትን ጉዳዩች ሞልታችሁ እንደምታነቡ በማመን ለኔ እንደሚታየኝ ከሶስቱ ብሄሮች፦ ኦሮሞ፣ አማራና ትግሬ የሚወለዱ የታሪክ ነጋሪያን እና አመስጣሪዎች እንዴት ታሪካችንን እንደሚያነቡት ላስረዳ።
===================
1 የአማራው ታሪክ ተንታኝ፦

የአማራው ታሪክ ተንታኝ በአመዛኙ የኢትዮዽያን ታሪክ የኔ ብሎ የሚያስብ፥ በሀገሪቱ በተካሄዱ መሰረታዊና ወሳኝ ጉዳዩች ላይ የራሱ ብሄር የተለየ ግዙፍ ሚና አለው ብሎ የሚያስብ፥ በመሆኑም በተነጻጻሪ አማራ ስልጡን ብሄር ነው ብሎ የሚያምን እና ለዚህ ተወልጄበታለሁ ለሚለው ብሄሩ አገር ግንባታ ታሪካዊ ሪከርድ ተጋድሎ ለመፈጸም የቆረጠ፥ ማን እንደኛ እያለ ማስረዳት እሚቃጣው፥ በዚህም የተነሳ ራሱን የተሻለና የዚሁ የተሻለው ታሪክ አድራጊና ፈጣሪ አድርጎ የሚያስብ ሆኖ የቆየ ነው።

አማራው እኮ ማለት የሚቀናው በቀጥታም አዙሮም የብሄሩን ታላቅነት ለመስበክ ወደሁዋላ የማይል ነው። የዚህን አገር ታሪክ የማንነቱ መገለጫና የአማራነቱ ክፋይ አድርጎ ስለሚያይ ብሄራዊ ማንነቱን ከታሪኩ ለይቶ ማየት የተሳነው ሊባል ይችላል። ይሄን ታሪክ ሊጠይቅ የሞከረውን ሁሉ ሀገራዊ ፍቅር የሌለው፣ ገንጣይ አስገንጣይ እያለ የሚፈርጅ ነው። የታሪክ አሳሳሉ ደግሞ አድናቂ እና አወዳሽ ከመሆን አይዘልም።

የዚህ የአማራ ታሪክ ተራኪ መሰረታዊ ስህተቶች ሁለት እንደሆኑ እረዳለሁ። አንደኛው የሀገሪቱን ታሪክ የአማራ ታሪክ ብሎ መውሰዱና ሁለተኛ ደግሞ የአማራን ማንነት እና ትልቅነት ከዚህ ታሪክ መወድስ ጋር አሰናስሎ የሰፋው መሆኑ ነው።

አማራው ከዚህም ታሪክ ጋር ይሁን አይሁን ክቡርነቱ እንዲያው ከተፈጥሮ እንደማንኛውም ህዝብ የሚቀዳ መሆኑን አይረዳም። በመሆኑም ለዚህ የታሪክ መምህር ታሪኩን መንካት አማራን መንካት፤ ይህን የሱን የታሪክ ትርክት አለመቀበል የአማራን የበላይነት እና የተሻሌነት አለመቀበል አድርጎ ይወሰደዋል። በቀጥታ ማንነቴ ተነካ ግን አይለንም። ሀገሬን ኢትዮዽያን የነካ እምዬ ኢትዮዽያን የደፈረ በሚል መፈክር ይህን የታሪክ ትርክት የተቹትን ያሳድዳል። ያኔም አሁንም።

በመሆኑም በኔ እምነት ሀገራዊ ታሪክ ሀገራዊ አንድነት እና ብሄራዊ ማንነቱ የተምታቱበት በመሆኑ የሌላውን የታሪክ ትርክት ለመስማት እንኳ እድል የማይሰጥ ይመስላል።

ንጉስ ሚኒሊክ ቅኝ ገዢ ወይስ ከፊውዳሎች እንደ አንዱ--- ክፍል 1




በመጀመሪያ ጉዳዩን ማየት የምፈልግበትን መነሻ ላስቀምጥ። አላማዬ ታሪካዊ ትንታኔ መስጠት አደለም። አላማዬ ታሪክ የምናጣቅስበትን መነሻና እሚመራበትን አተያይ መፈተን ነው። ለእናንተም በዚህ ንባብ ቃል እምገባው በየትኛውም ወገን ሆነን የሰማነውን ታሪክ መነሻ አላማና ግቡን እንድትጠይቁት የሚጠቁሙ ቁምነገሮች እንደማካፍላችሁ ነው።

ሀገራችን ከየት ናት? የመቼ ናት?

ሀገራችን የብራና መጻፍ ወይም አመተምህረት መጥቀስ ሳያስፈልግ ከሰሜን እስከ ደቡብ ህዝቡ ተሳስሮ የሚገኝበት አሰፋፈር አንዴ አንዱ ሲያይል ወደ ሰሜን ሲዘምት፤ ኦሮሞ ጎንደር ላይ ሆኖ ሲያስተዳድር እስከዛው ድረስ ያለውን ህዝብ በጦርነት ረምርሞት ሄዶ እንደነበር ይናገራል። እስከ ዛሬ ጎንደር ላይ የምናያቸው ስያሜዎችና አብያተ ክርስትያናት እና የኦሮሞ ባህልና ቋንቋ ያላቸው ማህበረሰቦች የሚያመላክቱት ያን ነው። በወሎ በኩልም የእያንዳንዱ ገጠርና ወንዝ አካባቢ ስም ሳይቀር በኦሮምኛ ተሰይሞ የምናገኘው በአጋጣሚ አደለም። አካባቢውን ይዞት ኖሮበት መርቶት እንደነበር የሚያሳይ ነባራዊ ሀቅ ነው። አሁንም ድረስ ኦሮምኛ የሚናገሩ የወሎ አካባቢዎች የዛ ዋቢዎች ናቸው። እስከ ትግራይ የኦሮሞ ባህል እና ደም አሻራዎች ዛሬም አሉ። እናም ሀገር አንዴ በሰሜኖቹ ተዋጊዎች ሌላ ግዜ ደግሞ በደቡቡ ጀግኖች ስትመራ ስትገብር የኖረችበት ሁኔታ ነበር። ሀገር አንዴም በደቡቦቹ ጭካኔ ሌላ ግዜ ደግሞ በሰሜኖቹ ጭካኔ ስትደማ ስትበለት ስትቆረጥ ነበር። 

የታሪክ ድርሳናት የቅርቡንም የሩቁንም ታሪክ ሲያወጉ የወንድ ብልትና የሴት ጡት ቆርጦ ወደ መጣበት አካባቢ በመውሰድ ጀግንነቱን የሚያስመሰክር ጦረኞች እንደነበሩ ይዘክራሉ። የገደልንም እኛው የተጋደልንም እኛው ማን ምንገደለ እንዴት ገደለም ብለን የምንነታረክ እኛው ነን። ታሪካዊ ሀቆቹን መቀየር አይቻልም። ሀቆቹን መካድም ፋይዳ የለውም።

ወሎ ካሳሁን ሁሴን የሚባል ሙስሊም ብቻ ሳይሆን መሀመድ ሀይለጊዮርጊስ አምባቸው ጉደታ የሚባልም ሰው ያለበት አካባቢ ነው። ስም እየጠራህ ስትሄድ ሀይማኖት ብቻም አደል የሚደባለቀው ዘሩም ድብልቅ ይሆንብሀል። ይሄን አገር በወጉ ካየነው ቋንቋዎቹ የሚያሳዩንን ልዩነት ሀይማኖቶቹ የሚያሳዩኑን መስመር እና ብሄራዊ ጥንቅሩ የሚያሳየንን ልዩነት ታሪካችንን የሁዋሊት እየተረተርነው ስንሄድ አናገኘውም።