Wednesday, December 19, 2012

ሙሰኞች ይውደሙ!? በቀረርቶ ወይስ በተግባር?

ሙሰኞች እና ሙስና የሚጎዳን መሆኑን እናውቃለን ግን እነሱ ለመስረቅ የሚተጉትን ያክል ለመታገል የሚተጉ አይታዩም

ሙሰኞች ይውደሙ ይጥፋልን -  እንራገማለን:: ሳይገባቸውም (ጠብቆም ሊነበብ ይችላል) መስረቅ ሽተው በአጭር መክበር አማሎዋቸው የበርካቶችን ስራ የማግኝት እና የመማር እድል የሚሰብሩ:: ሀብት የማፍራት ስራ የመፍጠር እና አገር የማገዝ ህልም ኖሮዋቸው የሚውተረተሩ ጎበዞችን የሚያንከራትቱ አላስፈላጊ ወጪ የሚያሶጡ ሌቦች በየግዜው ሲያዙም ያልተያዙትም በማስረጃ የሚያዙበት ቀን እስኪመጣ አክሳሪና አሳፋሪ ተግባራቸው በወሬ ሲነሳ እንሰማለን::

ሙሰኞች ከንቱዎች አሳማዎች ናቸው ማለት ግን ችግሩን የሚቀርፈው አይሆንም::

ሙሰኞች ገንዘብ ያስገኝ እንጂ በሌሎች ሞትም ቢሆን ከመክበር ወደሁዋላ የሚሉ አለመሆኑ መታወቅ አለበት:: ርህራሄ ያለመደ ባህሪያቸው ለሰው የሚገባውን ክብር የማይሰጥ ብቻ ሳይሆን ክቡሩን ሰው በመጉዳትም ጭምር ከመጠቀም ወደሁዋላ የማይል ነው:: በመሆኑም ሁሉም አማራጭ ለሙሰኞች ብሩን እስካመጣ መንገድ መሆኑን ይረዱዋል:: ለተራቡ ሰዎች የሚመጣን እህል ከመስረቅ በላይ የሚሆን አረመኔነት የለምና::

እናም ሲገባኝ ሌቦቹ ቁርጠኞች ናቸው:: የሙስናው ተቃዋሚዎች ግን በአመዛኙ በሰሞንኛ ወሬ ችግሩ የሚፈታ የሚመስለን የዋሀን ቢጤ ነን ወይም ደግሞ ሙስና ይውደም በሚል መፈክርና ርግማን አለያም በማያባራ የወቀሳ ጋጋታ የሚታረም ይመስለናል::

ተደብቀው የሚሰሩትን የሚያጋልጥ ማስረጃ የማይቁዋረጥ ክትትል አሰራሮችን የማሻሻል እና ለሌብነት ክፍተት የሚተው  አሰራሮችን እየደፈን መሄድ ይኖርብናል::

ለነፍስም ቢሆን ርህራሄ የሌለውን ሙሰኛ ተምሮ እና ስነምግባሩን አስተካክሎ እስካልመጣ ድረስ አንገት ላንገት ተናንቆ እንጂ በሰሞነኛ ርግማን ለመፍታት ማሰብ ወፈፌ የመሆን ያክል ይመስለኛል::

ሙሰኞች እንደ ጎልያድ ሊደልቡ እና ስባታቸው ሊያስፈራን ይችላል:: ቁምነገሩ ደፈር ብሎ የዳዊትን ጠጠር መጣል አለመጣሉ ነው::
ብዙ ግዜ ዳዊት የታለ? ማን ዳዊት ሆኖ ይታደገን? እያልን ስናላዝን ነው እነጎልያድ ይበልጥ እየሰቡ የሚሄዱት:: ፈረንጆቹ ለክፉዎቹ መንሰራፋት የመልካሞቹ አለመስራት ነው ምክንያቱ እንደሚሉት::

ቁምነገሩ ዳዊትን ራሱን ሆነን መገኘት ነው አለመስረቅ በአግባቡ በጎቻችንን መጥበቅ:: እነጎልያድ መንጋውን ሲያምሱት ደግሞ ጠጠራችንን አልሞ መጣል::

ዳዊትን ሻማ አብርቶ በቀን መፈለግ ሳይሆን የዳዊትን ባህሪ የተላበስ መልካም እረኛ አድርገን ራሳችንን መቅረጽ ነው መሰረታዊው ነገር::  ለጥቆ ዳዊቶቹን ማብዛት ይከተላል እነዳዊት በበዙበት ጎልያዶች ቦታ ስለማይኖራቸው::

የዳዊት ክብርና ሞገስ የደመቀው እና ለንግስና ያሳጨው  የጎልያድን ተግዳሮት በስኬት ሲወጣው ነው:: እኛም አገር መውዳዳችን እና ክብራችን እየደመቀ የሚሄደው ከፊታችን የተደቀኑ አገራዊ: ተቁዋማዊ እና ግለሰባዊ ችግሮችን በተሳኩ መንገዶች መፍታት ስንችል መሆኑ አያወያይም::

ሀቁ ይሄ ከሆነ ቁምነገሩ ችግሮቹን እና ፈጻሚዎቹን የመጥላት የማንቁዋሸሽ የማጣጣል አደለም የበላን ቦታ ላይ የሚያክ በርግጥም ችግሩን መፍታት የሚያስችሉ አሰራሮችን መዘርጋት እና ሌብነትን የሚጸየፍ እሴት መፍጠር ነው::

ርግማን እና ማጣጣል ንዶት የሚያውቀው የችግር ተራራ የለም:: ተግባር ግን ስንት ስኬቶች አስመዝግቡዋል::

No comments:

Post a Comment