Monday, December 24, 2012

አገራዊ ለውጥ ተቃዋሚዎችና ኢህአዴግ

የስራውን ውጤት ያለማንም ጣልቃ ገብነት ከጅምሩ ማጣጣም የቻለው ህዝብ በቅጡ በተደራጀ መልኩ ባይመራም ከሰማንያ አራት ጀምሮ እድገት ማጣጣም ጀምሮዋል፡፡ ተቃዋሚው ከሀዲ ስለነበር እንዲያውም ጨለመ እንኩዋንሰ ሊነጋ በሚል ስብከት ተጠምዶ የነበረ ቢሆንም፡፡

በሂደት ኢህአዴግ ፍልስፍናዎቹ እየተፈተኑ ጥቅል የአመራር እሳቤዎቹ ተጨባጭ ፖሊሲዎች ሆነው ብቅ ካሉበት ከ1994 ዓም ጀምሮ ግን አገር የተለየ ጎዳና ያዘች፡፡ ህዝብ ለውጡን ማጣጣም የሚችልበት እድል እንዳይኖር የተቃዋሚው ጎራ ጥቁር ጫጫታ በአንድ ወቅት እንዲያውም ወደ ነውጥነት ተመንዝሮ ሰላማችንን ክፉኛ የተፈታተነው ቢሆንም፡፡ 

በአንድ በኩል የአገር ውስጥ ተቃዋሚው ጭፍን ስብከት በልላ በኩል የውጪው ኒዮ ሊበራል ሀይል የኔን መስመር ካልተከተላቹህ በሚል ግትርነት የሚፈጥሩት ሰባራ ሰንካላ ስም ማጥፋት አገራችን በከባድ መስዋእትነት የጀመረችውን የልማት መንገድ ፈታኝ አድርጎት ነበር፡፡

በርግጥም ኢህአዴግ ግዜ የሚፈታውን ለግዜ ትቶ አይኑን ከተስፋ ሰጪ የልማት ስራዎቹ ሳይነቅል ተጉዝዋል፡፡ ፈረንጆቹ በየመንገዱ በሚጮህ ውሻ ላይ ሁሉ ድንጋይ እምትወረውር ከሆነ እምትሄድበት አትደርስም እንደሚሉት ሰዶ ማሳደድ አይኖርም በሚል ጽኑ እምነት ትኩረቱን በልማት ማፋጠንና ሰላም ማስጠበቅ ስራው ላይ አድርጉዋል፡፡ ይሄ ጉዞ እንደማንኛውም ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ሂደት ከፊቱ አቀበትና ቁልቁለት ያለበት ዛሬም በደረስንበት ደረጃ የሚፈተን ቢሆንም ከባዱን ግዜ ግን ይበልጥ ተምሮ ልማታዊ ልምዶቹን ቀምሮ ባለመቶ ፍሬዎቹን ሸክፎ ተሻግሮታል፡፡

አሁን አገር አላደገም የሚለው ተረት ሰሚ አጥቶ እድገታችን በየቢሮው ሹማምንት የሚቀቅሉት መረጃ (ኩክድ ዴታ) አለመሆኑን ህዝብ ከተጨባጩ ለወጥ አረጋግጡዋል፡፡ ኩክድ ዴታን እንደ ቃላት ክምችታችን እድገት ማመላከቻ መውሰድ ቢቻልም እውነታውን ማሳየት ግን አይችልም፡፡ ለዉጡ እና ፈጣኑ አመታዊ እደገታችን አንዳንድ ፖሊሲዎቻችንን ለማይቀበሉት እንደነ አለም ባንክ እና አይ ኤም ኤፍ በመሳሰሉም አለምአቀፋዊ ተቁዋማት ተመስክሮለታልና፡፡

እድገታችን እውን መሆኑ የሚታወቀው በነጭ ቆዳ የተመሰከረ ሲሆን በመሆኑ አደለም የነዚህን ተቁዋማት ምስክርነት የምንጠቅሰው፤ ይልቅም አገራዊ ተቁዋሞቻችንን ቁጥር ፈብራኪ አድርገው ለሚያዩዋቸው ወገኖች እውነታውን ከሆነ የሚፈልጉት ቢያንስ ቢያንስ ከሚያመልኩዋቸው የነጮቹ ሪፖርት እንዲያዩትም በማሰብ ነው፡፡ ችግሩ አለማቀፍ ተቁዋማቱም ቢሆኑ ስኬቶቻችንን የመሰከሩ ቀን ያው የተለመደ ፕሮፖጋንዳ ነው መባሉ ነው፡፡ የተቃዋሚው አጀንዳ ለውጥ ሳይሆን ማጠልሸት ብቻ ስለሆነ፡፡  

የባለፉትን ዘጠኝ አመታት የአለም ባንክን የኢኮኖሚ ሪፖርት ወስደን ስንገመግም አገራችን በ10.6 በመቶ ማደጉዋን ብቻ ሳይሆን አገራዊ ተቋሞቻችን ልማቱን በተመለከተ የሚሰጡን መረጃ እውነት እንደነበራና ይህም እምነት የሚጣልበት ተቁዋማዊ አሰራር እና አመራር ያላቸው መሆኑን እንደሚያመላክትም ነው፡፡ ከማደግም በላይ የሚበልጠውንና ነገ እንደምናስመዘግብ በርግጠኝነት  የምናልማቸዉን ትላልቅ የልማት ስራዎች በብቃትና በታማኝነት መወጣት የሚችሉ ተቁዋማት እንዳሉን ያረጋገጠም ጭምር ነው፡፡

እቺ አገር ገጽታዋ ይቀየራል የሚለውን ምኞታችንን ተሻግረን ገጽታዋ በፍጥነት እየተቀየረ መሆኑን ታዝበናል፡፡ ባለፈው አስር አመት ባስመዘገበችው እድገትዋ የአፍሪካ ታይገር ኢኮኖሚ መባል ችላለች፡፡ የአለም ባንክም በቅርቡ ባወጣው ሪፖርት ኢትዮጲያ ከቻይናዉያኑ ጋር የሚቀራረብ ከደቡብ ኮሪያና እና ታይዋን የቀድሞ ፈጣን እድገቶች የሚልቅ ባለ 10.6 በመቶ እድገት ከእኤአ 2004 ጀምሮ ባሉት ዘጠኝ አመታት ማከናወን መቻሏን አትቷል፡፡ ይሄ በታታሪ ህዝብና በጠንካራ መሪ ድርጅት የሚገኝ እንጂ አጋጣሚ አደለም፡፡

አገራችን የምትከተለው እድገት ምስራቅ ኤስያውያኑ ፈጣን ለውጥ ካመጡባቸው መስመሮች ጋር እንደሚመሳሰልም የአለም ባንክ ሪፖርት ያመለክታል፡፡ ስለ እድገቱ ተመሳሳይ ምስክርነት አይ ኤም ኤፍ እና ዘ ኢኮኖሚስት ይሰጣሉ፡፡ አገራዊ ለውጦቻችን በማጠልሸት የሚደፈቁበት እድል ፈጦ በወጣዉ ውጤት ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ ተደፍቁዋል፡፡ ነገ በሚመዘገቡ ትላልቅ ስራዎቻችን ደግሞ ይበልጥ ይደምቃል፡፡

ከላይ በቀረቡት መነሻዎች የተቃዋሚውን ጎራ ትርክቶች እንዳስ፡-

በመጀመሪያዎቹ አስር አመታት አገሪቱ የምትመራባቸውን ህጋዊና ተቁዋማዊ መደላድሎች በመፍጠር ስራ ተጠምዶ የነበረው ኢህአዴግ በሁዋለኞቹ አስር አመቶች ደግሞ የፖሊሲዎቹንና ተቁዋማዊ ለዉጦቹን ትክክለኝነት የሚያረጋግጡለት ጅምር ውጤቶች ማጣጣም የቻለ ቢሆንም፡
ተቃዋሚዎቹ ያለመታከት ሀገራዊ የልማት አቅማችንን ከኤርትራ ወደብ ጋር በማያያዝ አንገታችን ተቆረጡዋልና አክትሞልናል የሚል ዝማሬ ሲያቀነቅኑ ነበር፡፡ 

ወደብ በተጨባጭ ሁነኛ የልማት አቅም አለመሆኑ ቢታወቅም በዚህ ታርጋ ግን ቀላል ግምት የማይሰጠው ማምታታት ችለዋል፡፡ ይሁንና ልማታዊ አቅማችን ወደብ ሳይሆን ልማትን መተለምና መፈጸም የሚችል መሪ ድርጅት እና የፈጠራ ብቃቱ በቅጡ የተገነባ ሰብአዊ አቅም መሆኑን በማያወላዳ መንገድ ዛሬ ላይ በተግባራችን አረጋግጠናል፡፡ ትላንትናም በቃልና በመጻፍ የታገልነው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡

እንደሚሰብኩን ወደብ ሁነኛ ልማታዊ አቅም ሆኖ ቢሆን ኖሮ በውቅያኖስ ዙሪያ ያሉ ስንት የአፍሪካና የተቀረው አለም አገሮች ፈጣን ለውጥ ማስመዝገብ በቻሉ ነበር፡፡ የለሙት ሀገሮች ልማታዊ አቅም የለማና ትጉህ ሰብአዊ አቅማቸውና ይህንኑ በአግባቡ መምራት የሚችል ፖለቲካዊ መዋቅር ያላቸው መሆኑ ነው፡፡

አንዴ በተገኘሁበት ስብሰባ ላይ አንድ ጃፓናዊ ፕሮፌሰር ያሉትን ላንሳ፡- አንድ ኢትዮጵያዊ ዶ/ር ስለለውጥ ግብአቶች ሲያወሩ ፋይናንስ፣ የተፈጥሮ ሀብት በተጨማሪነትም የሰው ሀይል… እያሉ ማብራሪያቸውን ሲቀጥሉ ላስቁሞት ዶ/ር የሰው ሀይል ተጨማሪ አደለም የሰው ሀይል ወሳኙና ሁነኛው የልማት አቅም ነው፡፡ ሌሎቹ ይጨመራሉ፡፡ ጃፓንን እንውሰድ የተፈጥሮ ሀብት የላትም ግን ከና ከጥዋቱ የልማቱ ዋነኛ ምሰሶ መሆኑ እየተነገረው የሚያድግ ጠንካራና የፈጠራ ክህሎቱ የዳበረ የሰው ሀይሉዋን ተጠቅማ ሌሎቹን በሂደት እየፈጠረች ነው ያደገችው፡፡ ዋናው ከጃፓን የሚወሰደውም ልምድ ይሄው ነው ማለታቸውን አስታውሳለሁ፡፡

ኢህአዴግ በተግባር ወሳኙ የልማት ሀይል የፈጠራ ብቃቱ የጎለበተ የሰው ሀይል መሆኑን ገና ከጠዋቱ በመደምደም ይህንኑ የልማት አቅም ሳያሰልስ ለማነጽ ሰፊ ጥረት አድርጉዋል፡፡ ወደብን የተመለከተ ነገር በተነሳ ቁጥር አገልግሎት ነው እንገዛዋለን ነበር መልሱ፡፡ ወደብ ቢኖረው የሚጠላ የለም ከሌለ ደግሞ ወይ አሰብ እያሉ ማላዘን ሳይሆን ቁምነገሩ ዋናዉን የልማት ሞተር አንቀሳቅሶ ልማቱን ማንደርደር ነው ፡፡

ኢህአዴግ እንዳለውም አሰብ እኛ ባለመጠቀማችን የግመል ማጠጫ ነው የሆነው፡፡ ወደቡን ለማጣጣል አደለም:: በቁምነገሩ የሚሸጥ ያመረትነው ወጪ ምርት ሲኖር የምናስገባው ለልማታችን የምንሻው  ግብአት ሲኖር መሆኑን ለማመላከት ነው፡፡ የኤርትራ መንግስትና ተቃዋሚዎቹ እንደዘመሩት ኤርትራም አንገት እንዳልሆነች እኛም ራስ አልባ በድኖች እንዳልሆንን በተጨባጭ ባለፉት 20 አመታት ባስመዘገብናቸው ሁለንተናዊ ለውጦች ተግባራዊ ትምህርት ተወስዶበታል፡፡

እንደተባለው ወደብ ይቀይር ቢሆን ብዙ ሳንርቅ ኬንያ አስገምጋሚ ለውጥ ባመጣች ነበር፡፡ ሌሎቹም በምስራቅና ምእራብ አፍሪካ ያሉ አገሮች በለሙ ነበር፡፡ የለሙ አገሮች ኢኮኖሚያዊ አቅሞቻቸውን በቅጡ የተገነዘቡ ናቸው- አሜሪካዉያኑ ቅድሚያ የወሰዱበት የፈጠራ ክህሎታቸው፤ ጀርመኖቹ መሺኖች የማምረት አቅማቸው፤ ቻይናውያኑ ራሳቸውን የማኒፋክቸሪንግ ማእከል ማድረጋቸው፤ ጃፓናውያኑም ተመሳሳዩን ከቻይና ቀድመው መፈጸማቸው ነው ፡፡ ሌሎችም የለሙና በመልማት ላይ ያሉ አገሮች ሁነኛ የልማት አቅም የለማ የሰው ሀይል መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

ይሄ ያጡትን ለማጣጣል በማሰብ የሚደረግ መዋተት አደለም፡፡ ማንኛውም ልማታዊ አቅሞችን በተመለከተ መረጃዎችን የሚያገላብጥ ሰው ሊደርስበት የሚችል ሀቅ ነው፡፡ ይሄ ልምድ በተሳከረና ሚዛኑን በሳተ ግምቱ በወደብ ስም ኢትዮጵያን አንበረክካለሁ ብሎ ሲያስብ ለነበረው የኤርትራ መንግስትም የማያዳግም ትምህርት ሰጥቷል፡፡ በቀጠናው በርካታ ወደብ ከመኖሩ አንጻር የተሻለ አገልግሎት በተወዳዳሪ ዋጋ ማቅረብ ያለባትና በጋራ ተጠቃሚነት መርህ መስራት ያለበት አገልግሎቱን በማቅረብ ጥቅም የሚያገኘውም ጭምር መሆኑን ያመላከተም ነው፡፡

ነዳጅ እና ማዕድን አልባው ኢኮኖሚ ያለወደብ ባለ 10.6 በመቶ እድገት ያሰመዘገበውና ለሚቀጥሉት አመታትም በዚሁ ጥንካሬው እንደሚቀጥል የሚነገርለት ልማታዊ አቅሞቹን ለይቶ በትጋት ስለሰራ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል፡፡

አገር የሚከፋፍለው ጭራቅ የት ጠፋ!

አገር ይበትናል፣ ህዝብ ያባላል፣ ኢትዮጵያዊ አንድነትን ያጠፋል የሚባለው ፓርቲ ምን ውሀ በላው?! አገር ይኸው 20 አመት ይበልጥ በመንገድ፣ በቴሌኮም፣ በመብራት፣ በንግድ፣ በህብረብሄራዊነታችን በደመቀ የላቀ አንድነት፣ በተጡዋጧፈ ልማት ትጓዛለች፤ አገር የሚበትነውን ጭራቅ ታዲያ ምን በላው!?

ሲጀመር አገር ሊበተን ነው አንድነታችን ሊበረዝ ነው የሚለው ስብከት በተቃዋሚዎቹ ህሊና የተሳለ እና ለአንድነቱና ለአገሩ ደህንነት ትልቅ ግምት የሚሰጠውን ህዝብ ለማስቆጣት የተፈጠረ ነጭ ውሸት ካልሆነ በቀር፡፡ ባወሩት ቁጥር የበለጠ ለራሳቸው እውነት እየመሳለቸው የመጣ ለሀያ አመት ካካናወነው የተሳካ ሀገራዊ ለወጥና መግባባትም በኋላ፤ አንዴ እንጂ ሁሌም ሊሸውዱት የማይችሉትን ህዝብ ቢያንስ በአደባባይ ፕሮፖጋንዳ መሆኑን ባይነግሩት እንኩዋ ጎበዝ ለዛሬው ሁኔታ እውነት የሚመስል ተረት እንፈልግለት አለማለታቸው የሚገባቸውን እንኳ መስራት ቢሳናቸው ፕሮፖጋንዳም ከወቅቱ ሁኔታ ጋር እያስተያዩ የመቅረጽ ስንፍና የተጸናወታቸው መሆኑን ያመላክታል፡፡

ቢያንስ ቢያንስ ህዝብ ይሰለቸናል አዲስ ወሬ እንፍጠርለት እኮ ይባላል፤ የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ ሆነብን እኮ፡፡ ይሄ የመሀይማን ስብስብ የተባለው ፓርቲ አለምን ያነጋገረ እድገት ሲፈጥር ቢያንስ እኛ ሙሁራኑ እንዴት አዲስና ተቀባይነቱ ከፍ ያለ አነጋጋሪ ርእሰ ነገር መፍጠር ይሳነናል ብሎ ስብሰባ ማካሄድና መገማገም ይገባቸው ነበር፡፡

ጭራቁ ኢህአዴግ ከሆነ ደግሞ በቃልም በመጻፍም የተከራከረበትን በተግባር ባስመዘገባቸው ውጤቶች በርግጥም ጭራቅ እንዳልሆነ አስመስክሩዋል ብቻ ሳይሆን አገሪቱን በአለም ላይ ፈጣን አመታዊ እድገት ከሚያስመዘግቡ አገሮች ተርታም አድርስዋታልና ቢያንስ መልአክ ባይሆን እንኳ የትጉሀንና የብልህ ሰዎች ድርጅት መሆኑንም አረጋግጧል፡፡ እናም ቢያንስ ለዛሬ እንደ ምርጫ ምልክቱ ንብ የሆነና ለአገራዊ እድገቱ በአጭሩ ታጥቆ እየሰራ ያለ ፓርቲ በመሆኑ ሌላ ከወቅቱ ሁኔታው አንጻር በደካማነት የሚያስከስሰው ታርጋ ይፈልጉለት የሚል እምነት አለኝ፡፡

በቀጣይ ጽሁፌ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ጥያቄዎች ላይ ያሉኝን እይታዎች ይዤ ብቅ እላለሁ፡፡       

No comments:

Post a Comment